Monday, November 19, 2018

ስሜት ተጋሪዎች

ከድንክ አልጋዬ ላይ ህልም አይቸ ማታ
የባ'ል ገበያ ውስጥ የትዳር ገበታ
መበልት ወይዛዝርት ስሜት ተጋሪዎች
ፍቅርን በድቃቂ ሳንቲም  መንዛሪዎች
ምን አልባት ወደ ፊት ሴተኛ አዳሪዎች
ይህ አይመጥንሽም ይህም አይሆንሽም
ቅቅል አይጋብዝም ክለብ አያመሽም
ያኛው ዝምተኛ ዝጋታም ኮስታራ
ሁል ጊዜ ቁምነገር ቀልድ የማያወራ
ቀብራራ ገጠሬ ቪላ ቤት የሌለው
ገና በማህፀን አምላክ የበደለው
እያሉ በህብረት በማበር ሲዞሩ
በትዕቢት በጉራ እንደተወጠሩ
ከደራው ገበያ ጥሪት ሳይሸምቱ
በጠራራው ፀሐይ እንዲያ እንደዋተቱ
አንዳቸው ሳይዘግኑ ብፌው ባዶ ሆነ
ሰዓቱ መረሸ ገቢያው ተበተነ
ምሱ ፆም ማደር ነው
መውደድን በወረት በብር ለተመነ

ማሳሰቢያ : ህልሜ ወደ ትንቢትነት ከመቀየሩ በፊት ልብ ያለሽ ልብ በይ ።

Saturday, November 17, 2018

.....ላንቺ....


የብዕሬ ጠብታ ላንቺ የሚመጥን ባይሆንም ቀለሙ
በሄድሽበት ሁሉ እንድታስታውሽኝ እስከ ዘላለሙ 
ፃፍልኝ ያልሽኝን ያው ተቀኘለሁልሽ
በግሩም ተፈጥሮሽ ስፍስፍ ብልልሽ
መናኝ በሚያስቱ አስማታም  ጥርሶችሽ
ቀልብን በሚያሣጡ ምትሃተኛ ዓይኖች
አንኳን ሁለት ስንኝ እንኳን ስምንት ቀለም
ህይወት ብታስከፍይ ላንቺ ብዙ አይደለም
አይመረመሬው የሠራሽ ተጠቦ
የውበት ተምሣሌት ጠይም የደም ገንቦ
የሥብዕና ጥግ የሴትነት ልኩ
ምን ብዬ ልግለፅሽ እንዴው በምን መልኩ?
ታዲያ ለዚህ ገላሽ ለዚህ ውብ ተፈጥሮ
ስምሽ ግንባሬ ላይ በደማቅ ተወቅሮ
አገልጋይሽ ልሆን አምላክ ቢፈቅድ ኖሮ
ደከመኝ ሰለቸኝ አልልም  ነበረ
ዳሩ ምን ዋጋ አለው ምኞት ሆኖ ቀረ
©/ ጌታነህ ካሴ ኅዳር 7/2011 .

እንኳን ደስ ያላችሁ


ወንጭፋችን ባዶ
ጎልያድ ከማዶ
ከእጆቼ አታመልጡም እያለ ቢፎክር ቢሸልል ቢያቅራራ
በድሮ ልማዱ ከአሮጌ ሰማይ ላይ ነጎድጓድ ቢያጓራ
ደመና ፀንሶ እሣት ወይ ነበልባል በረዶም ቢያፈራ
ጦርነቱ ከባድ ቀበቶ ሚያስፈታ
የብዙ ጓዶችን እስትንፈስ የገታ
ለመግለፅ የሚከብድ ለወሬ አስቸጋሪ
በሩቁ ለሚያዩት ቢሆንም አስፈሪ
እኛ ግን ተርፈናል ይመስገን ፈጣሪ
አልሃምዱሊላሂ  ከፍ ይበል ንጉሡ
ምጡን እርሱትና ልጃችሁን አንሡ
ተደሰች ተደሰት ጨፍሩ ደንሡ
በአሸናፊነት  ድል ከፍ ይበል ጽዋችሁ
አቮ  ደስ ብሎኛል እንኳን ደስ ያላችሁ 
©/ ጌታነህ ካሴ ኅዳር 3/2011 ዓ.

Friday, September 28, 2018

ውረድ ከመንበሬ

ምነው ይጨንቀኛል ባርባር ይለው ሆዴ?
ትውልዴ ተቆጥሮ ልሳኔ ተጣርቶ ላይቀር መታረዴ
ምነዋ መስገብገብ ለነፍሴ መጓጓት መኖርን መውደዴ?
ወልዳ መሳም ላትችል ነፍሰ ጡሯ እናቴ
እስከ መቼ ድረስ
አንገቴን ላቀርቅር ይንበርከክ ጉልበቴ
ሰላም ላውርድ ብዬ ሀገር ላቅና ብዬ
ፈገግ ብዬ ባቅፍህ ደስ ያለኝ መስዬ
ያረድኸው ወንድሜ ደሙ ሲከረፋኝ
መግደል መሸነፍ ነው ብለህ ብትደልለኝ
እንዴት አልናደድ እንዴትስ አይከፋኝ
እንዴት አይዘን ልቤ እንዴት አይገምልለኝ
በርግጥ አውቂያለሁ ገብቶኛል ጥፋቴ
ሀገሬን ለቁራ አደራ መስጠቴ
የቁራ ልጅ ቁራ ቁራ የወለደው
ከመገንባት በፊት ማፍረስ የለመደው
አመራር ላስተምር አገዛዝ ላለምደው
ሀገር አቅና ብዬ መንበር ላይ ብጥደው
መሰረቱን ጣለ
ቤት ሊሰራ ነው ስል ያው መልሶ ናደው
የባለጌ ክንዱ ቢሆንም ደንዳና
ማፈራረስ እንጅ መስራት የት ያውቅና
የጋለሞታ ልጅ ያልተቆነጠጠ
ተለቅቆ ያደገ ተሳድቦ እየሮጠ
አጥፍቶ በመጥፋት ሆኖ አስተዳደጉ
መናድ ይመስለዋል  የነጻነት ጥጉ
ውረድ ከጫንቃዬ ከእንግዲህ  ይበቃል
የሚያጠግብ እንጀራ ሊጡ ያስታውቃል
እርካቤን ወዲህ በል ውረድ  ከመንበሬ
አርማዋ ከፍ ይበል በደም ያቆየኋት ኢትዮጵያ ሀገሬ
 ኪቶመስከረም 8/2011 .

Monday, August 20, 2018

እንትን አፍጥ

 
አሁን የቆምሁባት ተራራ እንትን አፍጥ ትባለለች። “ተራራ ሲወጡ የሚፈጥባቸው ነገር አለ እንዴ?” የሚለውን ጥያቄ ለሴቶቻችን እንተወውና እዚች ተራራ ላይ ቆሜ አንድ ጊዜ ወደ ላይ አንድ ጊዜ ወደ ታች እያፈጠጥሁ ነው። የሚታየው ሁሉ እጅግ ይማርካል ሊያዘረዝር የተዘጋጀ የገብስ ቡቃያ፣ የተዳገረ ቦቆሎ፣ የለሰለሰ የጤፍ መሬት እርሻ ። ኧረ በወላዲተ-አምላክ እዚጋ ደግሞ በግራ ጎኗ እቅፍ ሙሉ እንጨት የያዘች ልጃገረድ፣ በአርባ ሽንሽን ቀሚስ ውስጥ ከፍ ዝቅ የሚል ትልቅዬ መቀመጫ፣ያለ ጡት ማስያዣ የቆመ አጎጥጎጤ ጡት፣ ሊፕስቲክ አይቶ የማያውቅ ሳሙኝ ሳሙኝ የሚል ከንፈር፣ ፣ የሚሽኮረመሙ ዓይኖች ፣ ባለ ዲምፕል ጉንጭና ባለ ንቅሳት ግንባር ወይኔ ቀጭኑ ማበዴ ነው መሰል!
በመሄድና በመቆም መሀል ፈዝዠ ይኸን ሁሉ ስመለከት የመነኩሴ ምራቅ የሚያህል የዝናብ ጠብታ መሀል ጆሮዬ ላይ ሲላተም የፈጠረው አሰቃቂ ድምጽ ከቁም ቅዠቴ ቀሰቀሰኝ። ድምፁ ሁሉንም የታች ቤት ነዋሪዎች ያስደነገጠ ነበር። አንዳንድ ቧልተኞች እንደሚሉት ከሆነ አማኔ ሊጠጣ ወደ አፉ ያለውን ቡና መልሶ “እሰይ አትሂድ ስለው ሲንቀለቀል ሂዶ አስገቡለት” ሲል ሰምቶ አንቱካ ምናባህ በማለት ተቆጥቶታል። መሲና ቅድስቴ ጸሎት ቤት ውስጥ የድንግል ማርያምን ሥዕለ አድህኖ ታቅፈው ተገኝተዋል። እንዳሌና ሲስተር አዘነጋሽ በአርምሟቸው ፀንተው ያሳለፉት ሲሆን ረቂቅ “ውይ ጌችዬን ምን ነክቶብኝ ይሆን” የሚል ቃል አምልጧታል። ስሌሎች የተጣራ መረጃ አላገኝሁም። እኔስ ምን ሆንሁ? እኔማ ወንድነቴን ልጅቱ እንድታይልኝ ፈልጌ ይሁን የአዲስ አበባው ጉዴ ትዝ ብሎኝ “ዘራፍ የበላይ አሽከር” ብዬ አካባቢውን ስቃኝ ማንም አልነበረም።
ባለፈው ቅዳሜ ዕለት አ.አ ከአውቶብስ ተራ ወደ ጎጃም በረንዳ በሚወስደው መንገድ እየተጓዝሁ አንዱ ሰላቶ በቀኝ ጎኔ በኩል (ያባቴ አምላክ ጎኑን ይንቀለውና) በጫማ ጥፊ መታ መታ ሲያደርገኝ ፊቴን እንደ መከራ አጥቁሬ ከፈረስ ጭራ በቀጠነ ድምጽ ስልኬስ አልሁት በግራ ጎኔ የቆመውን ግሪሳ። የፊቴ መኮሳተር አስፈርቶት ይሁን የድምፄ መቅጠን አሳዝኖት አላውቅም እሽ ብሎ ስልኬን መለሰልኝ። እኔም መንገድ ዳር ወድቆ ከማደር የጠበቀኝን አምላክ እያመሰገንሁ ወደ አዲሱ ገበያ በታክሲ። ከቅዳሜው ትዝታየ ስመለስ ልጃገረዲቱም ከአካባቢው ተሰውራለች። ዝናቡም መጣሁ መጣሁ ይላል፤ ጉርጥ ጉርጥ የሚያህል የዋልካ ጭቃ እየዘለለ ቦት ጫማየ ውስጥ ይከተታል፤ እኔም ጉዞዬን ቀጥያለሁ።“ጉች ጉች ያለ ጡት በል ደህና ሰንብት አንተን ማግኘት ርቋል ከዕለተ ምፅዓት” የሚለውን ዘፈን እያንጎራጎርሁ።
ሾላሜዳ:ሐምሌ 13/2010ዓ.ም

Wednesday, July 11, 2018

የጋብቻ ጥያቄ

ቀን 3/11/2010 ዓ.ም
ለፕሬዝደንት ኢሳያስ አፈወርቂ
አስመራ


                 ጉዳዩ፦ የጋብቻ ጥያቄን ይመለከታል
እንደሚታወቀው እኛ ኢትዮጵያውያን እና ኤርትራውያን በኢኮኖሚ፣ በባህል፣ በጋብቻ የተሳሰረ የረጅም ጊዜ ታሪክ ያለን
ህዝቦች ነን። ከዓመታት በፊት በሁለቱ ህዝቦች መካከል የተፈጠረው ግጭት ወይም አለመግባባት የብዙ ወጣቶችን ህይወት
የቀጠፈና ደም ያፋሰሰ እንዲሁም ሁለቱን ህዝቦች ፊት ያዟዟረ ቢሆንም፤ በቅርቡ የተጀመረው ጥላቻን በምህረትና በይቅርታ
የመሻር ሂደት ሁላችንንም የደስታ እንባ አስነብቶናል። እኔም ዶ/ር ጌታነህ ካሴ የተባልሁት ግለሰብ በጅማ ዩኒቨርሲቲ
የህክምና ማዕከል የመጨረሻ ዓመት የህክምና ተማሪ ስሆን በክቡር ዶ/ር ጠቅላይ ሚኒስቴር ዓብይ አህመድ የተጀመረውንና
በሃገር አቀፍ ደረጃ ጎልቶ በመታየት ላይ ያለውን የሰላም፣የፍቅርና የመደመር መርህ እንዲሁም የህዝብ ለህዝብ ግንኙነት
የበለጠ ለማጠንከር ሁለቱን ህዝቦች ልብለልብ ለማስተሳሰር ክቡርነትዎ የጋብቻ ጥያቄዬን ተቀብለው አንዲት ውብ ሰሜናዊት
ኮከብ ጽብቅቲ ዓይናማ ሹርቤ ቆንጆ ልጃገረድ ይሰጡኝ ዘንድ በትህትና እጠቃለሁ።
ከሰላምታ ጋር
              ዶ/ር ጌታነህ ካሴ(MI)
       ጅማ ኢትዮጵያ

ግልባጭ
ለኤርትራውያን ልጃገረዶች በሙሉ

Monday, July 09, 2018

ቅኔ ነሽ

የጠገበው ሲሄድ የራበው ሲመጣ
ሲስተር አ'ዘነጋሽ ምጣድሽ አይውጣ
የሚል ግጥም ልፅፍ ልቀኝ ያመረኝና
ቃላት አቅም አጥተው ይሆናሉ መና
የማምዬን ናፍቆት ፍቅርሽ የሚያስረሳ
ለቁርስ የጋገርሽው የሚተርፍ ለምሳ
በፈተና ብዛት ትጥቅሽ ያልተፈታ
የጠላትን ጉራ ትዕግስትሽ የረታ
የሥጋ ፍላጎት ደፍሮ ያልፈተነሽ
ረሃብ ውኃ ጥም ያላመነመነሽ
ወርቅሽ ያልተፈታ አንች እኮ ቅኔ ነሽ
ታችቤት : ሰኔ 30 /2010 ዓ.ም
 እንኳን ደስ ያለሽ ለማለት ያህል

ልቤን አታድርቀው

ግድፈት የሌለበት እውነት መናገሬን ልብህ እያወቀው፣
እገሊት ከፍቷታል ያ ጎረምሳ ዝቷል በሚል እንቶ ፈንቶ ልቤን አታድርቀው።
አንተን ብሎ ትሁት ገልጋይ ደም አድራቂ፣
አንችን ብሎ ሸምጋይ ድንቄም አስታራቂ፣
ፍቅር ያሸንፋል በሚል የምፀት ቃል ከምትሳለቂ፣
ተመሳስሎ ኗሪ የቀበሮ ጃኬት ካፖርትሽን አውልቂ ።
እውነቱን ተናግረሽ ስትሄጅ ቢመሸብሽ ከዛፍ ስር እደሪ፣
ከትንሹ እግዚአብሔር ከህሌናሽ ጋራ በሰላምሽ ኑሪ።
ከራድዮን 28/10/2010 ዓ.ም

ረቢ

ሆላ መምህር ሆላ፣ ሆላ ረቢ ሆላ ፣
እየሱስ ክርስቶስ በተጠራበት ስም የተጠራህ ሁላ!
መምህር ሆይ
ይህን ሁሉ ዘመን ደብተር ተሸክሜ፣
ዘመኔን ቆንጥሬ እድሜየን ዘግኜ፣
ቀኔን አባክኜ ከፊትህ ታድሜ፣
ሌጣ አዕምሮዬን ለፍርጃ ሰጥቸህ፣
በገማ ቴዎረም በበሰበሰ ቃል ሞልተኸኝ ሰለቸህ።
በዚህ ሁሉ ዘመን
እድሌ ተስፋዬ ባንተ መዳፍ ወድቃ፣
አንተን በማዳመጥ ነፍሴ ማቃ ማቃ፣
የዛሬ እልፍ ዓመት በወጣ መረጃ፣
እውቀቴ ብቃቴ ባንተ ተፈርጃ፣
ይህን ሁሉ ዘመን
አንተ እኔን ብቻ ስትፈትን ስትለካ ፣ስትፈትን ስትለካ፣
የመንገዴ አቅኚ የጨለማዬ ጦር እያልኩህ ስመካ፣
ውሉ ሲመረመር የሆንህበት ምስጢር የህይወቴ ሳንካ፣
ወድቀሃል ያልኸኝ ለት፣ ሚዛንህ ሚዛኔ ሰባራ ነው ለካ።
ቀድሞስ አንስታይን መች ባንተ ተለካ!
ራስህን ስፈር፣ ራስህን መርምር፣ ራስህን ለካ።
ሆላ መምህር ሆላ፣ ሆላ ረቢ ሆላ ፣
እየሱስ ክርስቶስ በተጠራበት ስም የተጠራህ ሁላ!
እኔን ብሎ ሰሚ አንተን ብሎ ብርሃን ድንቄም መምህር እቴ!
ይህን ሁሉ ዘመን እድሜዬን ቀንጥሼ እኔን በመስጠቴ፣
ደንቆሮ ስትለኝ አንተን አይጨምርም እስኪ እንደው በሞቴ?
ሆላ መምህር ሆላ፣ ሆላ ረቢ ሆላ፣
እየሱስ ክርስቶስ በተጠራበት ስም የተጠራህ ሁላ!
እነ ዛራ’ስቱራ፣ እነ ክሪሽና
ሶቅራጥስ፣ፕሉቶ፣ እየሱስ ክርስቶስ ባለፉበት መንገድ፣
የምትንገዳገድ የምትወላገድ፣
ትውልድ የምትገድል በቅምጥ “ጀኖሳይድ”
ሆላ መምህር ሆላ፣ሆላ ረቢ ሆላ፣
እየሱስ ክርስቶስ በተጠራበት ስም የተጠራህ ሁላ።
ይህን ሁሉ ዘመን አድምጨህ አድምጨህ
ተስፋየ ካጨጨ ካጣሁ አንድም መላ፣
ወድቀሀል ብለሀል መቼስ አታስፈጨኝ ከእንግዲህ በኋላ።
ሆላ መምህር ሆላ፣ ሆላ ረቢ ሆላ፣
እየሱስ ክርስቶስ በተጠራበት ስም የተጠራህ ሁላ።
አርባ ‘ምስት ደቂቃ አርባ ‘ምስት ደቂቃ፣
እየተሰፈረች እድሜዬ ተሰረቃ፣
አስተምረኝ ብዬ ራሴን ሰጥቸው ነዝንዞኝ ሲያበቃ፣
ደግሞ ሌላ ነዝናዥ ጠመኔውን ይዞ ሲያስረኝ በፈረቃ፣
እንዲህ እንዲህ ተብላ ዘመኔ ተፍቃ፣
ሰሌዳ ሆኛለሁ ከእንቅልፌ ስነቃ።
ራሴን አገኘሁ ሆኘ ሰባራ እቃ።
መምህር እሽሩሩ፣
መምህር እሽሩሩ፣
ውረድ ከጀርባዬ እንግዲህ ይበቃል፣
ራሱን አስተምሮ አንስታይን ይነቃል።
ምንጭ፦ የቀንድ አውጣ ኑሮ በይስማዕከ ወርቁ

Sunday, June 17, 2018

የካፊያ ምች

 ተፈሪ ዓለሙ(1974)
ሳልላክ ተልካ እንሂድ አለቺኝ
ካላጣችው ሰዓት ከቤት አስወጣችኝ
ጥርቅም እቅፍ አድርጋ በካፊያ ሳመቺኝ
የእድሜ ልክ ልክፍቱን ያኔ አስለከፈችኝ
መብረቅ እየጮኸ ዝናብ እያካፋ
የእኔ ልብ በሷ የሷ በእኔ ጠፋ
የሰማዩ ባህር ቁልቁል ተንዶብን
ውሃ ጠማኝ ውሃ እየዘነበብን
ጠፍቼ ስመለስ ከእቅፏ ስወጣ
በርዶኝ አተኮሰኝ እቤቴ ስመጣ
እያደር አደረ ከርሞ ከረመብኝ
የዘመን ህመሜን ያን እለት ታመምኩኝ
አሁን አሁን ታዲያ!
ደመናው ሲጠቁር ነጎድጓድ ሲያጓራ
ነፋስ ሲያጉረመርም ክረምቱን ሲጠራ
ግንቦት ማለቂያ ላይ ይነሳል ህመሜ
ሲያቀብጠኝ በዝናብ በካፊያ ተስሜ
..........................ምች ተሳልሜ

የኔ ግን መለከፍ

ገና ከሩቅ ሳይሽ ይድናል ህመሜ
ብሞትም አይቆጨኝ ከንፈርሽን ስሜ
ባለንጋ ጣቶችሽ የዳበስሺኝ እንደው
እንደ ቶን እሳት ነው ውስጤ የሚነደው
ዳሌሽ እየኮራ ባትሽ ላይ ሲሳለቅ
እኮሰምናለሁ እንደመታው መብረቅ
እያለ ይገጥማል እያለ ይፅፋል
መልዕቁን ዘርግቶ ቁንጅናን ይቀዝፋል
ገጣሚው ዘንድሮ በውበት ተለክፏል
የኔ ግን መለከፍ በዳሌዋ አይደለም በሚሞናደለው
በፀጉሯም አይደለም እንደ ሐር ነዶ በተዘናፈለው
አይደለም በጡቷ እንደ ሚዳቆ ልጅ ላይ ታች በሚዘለው
በጥርሷም አይደለም እንደ ፀሐይ ጮራ በሚንቀለቀለው
እኔ ቀልቤን ስቼ በድን የምሆነው
መብረቅ እንደመታው የምኮሰምነው
ጀግንነቴ ከድቶኝ ትቶኝ የሚተንነው
ኧረ አንተው ለምን አልህ? በሚል ለዛዋ ነው
Dialysis room 06/10/10
በከፊል ከሄኖክ ብርሃኑ የተሰረቀ

Monday, June 11, 2018



ቃሊቲ ማረፊያ ቤቴን ሳያፈርሰው
እስረኛዬን ሁሉ ፈቶ ሳይጨርሰው
ጅምሩ አልጣመኝም ተው በሉት ይሄን ሰው
ታላቁ መሪ ¡ ከገሀነም

ጀግና ነኝ

የሚያምነኝ አይኖርም ይኸንን አውቃለሁ
ለራሴ እውነት ከሆንሁ እኔው እበቃለሁ
ሽንፈቴን አምኜ እንቅልፍ የማልተኛ
በአባቴ የወጣሁ ጀግና ነኝ ነፍጠኛ
ትምክህተኛ አትበሉኝ መመካት ያንሰኛል
የእሣት ልጅ ነበልባል መሆን ያኮራኛል
ልክ እንደ አባ ኮስትር እንደ በላይ ሁላ
ካሰብሁበት ሳልደርስ ትጥቄ የማይላላ
የግዮን መፍለቂያው ግሽ አባይ ሰከላ
ጎጃም ያበቀለኝ ዱር ቤቴ ዳንግላ
እንደ አንበሳው ቴዲ እንደ እሣቱ ረመጥ
ለሃይመኖቴ ሟች ማተቤን የማልቆርጥ
ዋሽቶ ከመሸለም ከርቸሌ የምመርጥ
የአባቶቼን ርስት ለባንዳ የማልሰጥ
እኔ ጾም እያደርሁ ለራበው የማጎርስ
ክፋት ምቀኝነት ከደጄ የማይደርስ
ብሉልኝ ጠጡልኝ የሆነ ልማዴ
ጎንደር ያሳደገኝ ወልቃይት ጠገዴ
ጀግና የጀግና ዘር አይደለሁም እንዴ?
ጌች ቀጭኑ 27/09/1ዐ

ዮርዳኖስ

ብዕርህ እረፍት ትጣ ታልቅስ ለምትሉ
እሪታ ዋይታዋን ይኸው ተቀበሉ
ለእኔ ያላት ፍቅር እጅግ ቢረታ
እናቴ ቤት ዋለች ከሰው ተለይታ
ክቡር ማህፀኗ ዮርዳኖስን ሆነ
ደማቅ ፈገግታዋ ከፊቷ ተነነ
የሞቀው ትዳሯ ቤቷ ተበተነ
ኤጭ
አቮ የምን ዋይታ
የምን እየየ ነው የምን እንጉርጉሮ
መፍትሔው ከደጃችን እያለ ከጓሮ
ይልቅ ሾፌር ንዳ ይፍጠን አንቡላንሱ
ችግር ሳይወለድ መዘዙ ሳይመጣ
በር የተዘጋበት በመስኮት ሳይወጣ
የሽንት መቋጠሪያ ሸምቀቁ ሳይላላ
የምጥ ጊዜ መርዘም ሳይፈጥር ፊሰቱላ
እናትና ልጁ ሆስፒታል ይድረሱ
15/09/10
መልካም የፊስቱላ ቀን ይባላል እንዴ?

Saturday, May 12, 2018

ያማል 3

እና እደነገርሁሽ
የረዚደንት ቁጣ አይቶ መሳቀቁ
ሲኔር መጣ አልመጣ ሰውነት ማለቁ
ፖርተር ማፈላለግ ከነርስ መዳረቁ
ዱቲ አድሮ ለሞርኒንግ ሽር ጉድ ማለቱ X ray ማስነሳት BF ማሰራቱ የወለደች እናት ጫማ መፈለጉ ሞቶ የወጣን ፅንስ "alive" ማድረጉ
ያለ ዲሰፖዜብል ቪጎ ማስተካከል ካቴተር መንቀሉ የደሞዝ ቅናሹን አምኖ መቀበሉ ምን ብዬ ልንገርሽ ያማል ይሄ ሁሉ ታማሚ አስታሚ ወላጅ አስወላጁ አጥማቂ ሰቫኪው አስቀዳሽ ሰጋጁ የፈቃድ ባርነት በአንድነት ሲያውጁ ጨካኝ በበዛባት በዚች የምጥ ዓለም
ከዚህ የበለጠ ሌላ ህመም የለም
ጌች ቀጭኑ ዘታችቤት 02/09/10

ጭቅጭቁ ያማል
ንትርኩ ያማል
በዚህ ሁሉ  መሃል
ምርኮኛሽ  ጧት ማታ ከደጅሽ ይቆማል
በርሽ  ተንበርክኮ  ብሶቱን  ያሰማል
የሠናፍጭ ቅንጣት በምታክል እምነቱ  ተራራው ይገፋል
የማያልፍ ቀን የለም የጭንቁም ቀን ያልፋል
ይሄን ጊዜ ታዲያ
የማረክሽው ልቤ እርጥብ በሚያቃጥል የፍቅርሽ ነበልባል
ፀጉሩ ያላረረ የእንባ መስዋዕትን ለክብርሽ  ያቀርባል
እና እንደነገርሁሽ እኔ አንችን ስወድሽ
ይኸን ሁሉ ችዬ ነው የምላመድሽ
እና እንደነገርሁሽ
የ“quali” ማዕበል  ወጀቡ ቢንጠኝ
ዓመት ሙሉ አንብቤ grade C ቢሰጠኝ
ችግር ቢደራረብ መከራ ቢበዛ
ማርክ በዳሌ ቢሆን  በከንፈር ቢገዛ
እኔ አንችን ስወድሽ
ይሄን ሁሉ ችዬ ነው የምሳደድሽ
ኦ እናት medicine ፀሊም ወፀዓዳ
ጽዋሽ የማያልቀው ቢቀዳ ቢቀዳ
መዛመድ ሳያንስሽ ተግባርሽ የባዕዳ
ከጦርነት ማግስት ቦምብሽ ሚፈነዳ
ኦ እናት medicine እናት ህክምና
ይሻልሻል ብዬ ከአምና ከታቻምና
ወጣት ልጅነቴን
ክብር ማንነቴን
ቆንጥሬ ሳላስቀር ጠቅልዬ ሰጥቸሽ 
ገዝግዘሽ ገዝግዘሽ ቆርጠሽኝ ሰለቸሽ
ኦ እናት medicine ፀሊም ወፀዓዳ
መዛመድ ሳያንሰን ተግባርሽ የባዕዳ
የዓርነቴ ፀሐይ የነፃነቴ ጎህ እያልሁሽ ስመካ
ፍቅርሽ አሲምፕቶት የሚጠጉት እንጅ በዕጅ የማይነካ
ጎጻጉጽሽ ብዙ ቢሆን  በዚች  ዓለም
እኔ አንችን  ከመውደድ የሚያግድ አይደለም

Tuesday, May 08, 2018

ተፈስሒ በሏት

ፀሐይን  የምትወልድ ውብ ደማቅ ጨረቃ፣
ቀድመው ያኸለሟት ቴክታና ጴጥርቃ፤
እናትና ገረድ ድንግልና ሰማይ፣
ሐመልማልና እሣት ሐርና ወርቅ ፈታይ፤
መሰረታቲሃ ውስተ አድባር  ውእቱ፣
ብሎ ያወደሳት ዳዊት በትንቢቱ፣
ተወልዳለችና የአምላክ እናቱ፣
ከበሮ ይመታ ይድመቅ ማኅሌቱ።
ጠላት ኃይሉን ይጣ ይንቀጥቀጥ ዓለሙ፣
የሕርያቆስ  ልጆች ድምፃችሁን አሰሙ፣
ተፈስሒ በሏት ካህናት አዚሙ።
ትንቢት  ተፈፅሟል ያስተጋባ ቃሉ፣
ተወልደ ብዕሲ በውስቴታ በሉ።
ጌች ቀጭኑ ዘታችቤት ግንቦት 1/2010 ዓ.

በለቅሶ  ሚዘሩ በደስታ  ያጭዳሉ፣
ብሎን  ነበር  ንጉሥ በማይሻር  ቃሉ፤
እንባችን  ፍሬ አጣ ዋይታችን መከነ ፣
ምነው  በኛ ዘመን ትንቢት  ቅዠት ሆነ?

ከተኩላዎች መሃል

በንፁህ  መነጽር ማስተዋል ለቻለ፣
ለአቤል  መስዋዕትነት  ቢላው  የተሳለ፣
ከተኩላዎች መሃል ንጹህ  በግም አለ።
እርም አርጎ ትቶ ጥንብን  ለጥንብ አንሳ፣
ወደ ላይ ለመምጠቅ ክንፉን የሚያነሳ፤
ብቻውን  የሚኖር በጆፌዎች መንደር፣
ለአመነበት ጉዳይ የማይደራደር፤
ስለ ድንቅ ብቃቱ  ብዙም ያልተባለ፣
በቁራዎች ሰፈር ነጭ ንሥር አለ።
ይውጠው  ይመስል  ድንቁርናን ቁጣ፣
አባት ለገደለው የልጅ ልጅ ሲቀጣ፤
ቀድሞ ሰው መሆኑን አውቆ የተረዳ፣
ታናናሾቹ  ላይ  ደርሶ   ማይፈነዳ፤
አውቆ ለማሳወቅ ሁሌም  የሚተጋ፣
በጎሜ በነገር  ሰውን  የማይወጋ፣
ከእግዜር  የተቸረ በፀጋ ላይ ፀጋ፤
ስሜትን  የሚያድስ የጥርሱ  ፈገግታ፣
ሰው  አየሁ  በህልሜ ትላንትና   ማታ።
ገጾች  ስገለብጥ  በህልሜ  መዳፍ ላይ፣
እንደዚህ የሚል  ቃል ይነበባል  ከላይ፤
እንደ ሣተኖቹ አንተም ሁን  ሣተና፣
እኩል  የፈጠረህ  የአዳም  ዘር  ነህና።

Ped OPD ይካቲ 17/2010 ዓ.ም ከሌሊቱ 7:30 ተፃፈ

Thursday, February 22, 2018

ልጆች ልከን ነበር

ልጆች ልከን ነበር ከተማ እንዲማሩ፣
ጨለማው ኑሮአችን በእውቀት እንዲያበሩ።
እነሱ እቴ ምርጦች ከሰው የተለዩ¡
እንኳን ቀለም ዘልቀው እውቀት ሊገበዩ፤ 
ያጵሎስ የጳውሎስ ብለው ሲለያዩ፣ 
የእምነት ቃላቸውን በክህደት ለውጠው፣
በብልጭልጭ ነገር በደስታ ተውጠው፣
በትምክህት በኩራት እንደተወጠሩ፣
የከፈቱትን በር ሳይዘጉት አደሩ፤
በሄዱበት መንገድ ሳይመጡበት ቀሩ።
አሁን ግን ነቅተናል ዘይደናል መላ፣
ማን ቁማር ይበላል ከእንግዲህ በኋላ?
ሴቷን በሚስትነት ለጦፈ ነጋዴ፣
ወንዱንም ማስጠበቅ ገዝቶ የበግ አዴ።
Farmed : 23/05/2010 ዓ.ም

Saturday, January 06, 2018

ሲዋንን ያለፈ

ከሰላም እንቅልፉ  ከምትቀሰቅሰው፣
ጓደኛህን በቁም አሁን  አሞጋግሰው፤
ብላ በምትመክረኝ በቀይዋ ብዕሬ፣
በጥዋት ተነሳሁ ላሞካሽህ  ዛሬ።
ልክ እንደ አባ ኮስትር እንደ በላይ ሁላ፣
ካሰበበት ሳይደርስ ትጥቁ የማይላላ፣
ያበቅላል ወንድ ልጅ ዱር ቤቴ ዳንግላ።
አንዱ በሃይማኖት ሌላው በሰፈሩ፣
አንገቱን ሊያስደፉት  ሲለፉ ሲጥሩ፣
ገድለው ሊያዳፍኑት ጉድጓድ ሲቆፍሩ፤
ጀግና የጀግና ዘር መሆኑን ሳያውቁ፣
በቆፈሩት ጉድጓድ እየገቡ አለቁ።
የጎጃም እናቱ አትውለጅ ምከኝ፣
እንደ በላይ ጀግና ከንቱ ላታገኝ።
የሚል ጎጅ ምክር አልመክርሽም እኔ፣
በፍቅሩ ሰው ገዳይ እያየሁ ከጎኔ።
አርግዥ እንጅ ጸንሽ ውለጅ መንታ መንታ፣
ተከብሮ  ሚያስከብር በቆመበት ቦታ፣
አውቆ የሚያሳውቅ ተሟግቶ ሚረታ።
ጀግንነትን በጦር ያደረገው ማን ነው?
ወንድነትን በሰይፍ ያደረገው ማን ነው
?
ወድቋል በቃ ሲሉት
ሲዋንን ያለፈ ለእኔ እሱ ጀግና ነው።
ጅማ ጤና ጣቢያ: ታኅሣስ 13/2010 .