Sunday, November 19, 2017

ሐዋርያት

ኑሮን ለማሸነፍ ቤተሰብ ሊመሩ
ከላይ ታች ብለው ሲለፉ ሲጥሩ
በየሥራ መስኩ ከተሰማሩበት
መርጦ ቢጠራቸው ጌታ ለአገልግሎት
ቤትና ንብረቴን ወገኔንም ሳይሉ
ሁሉን ንቀው ትተው አምነው ተከተሉ
በዋለበት ውለው ባደረበት ሲያድሩ
ድንቅ ተዓምራቱን ማዳኑን   እያዩ፣
በሃይማኖት ጸንተው በእምነት ጠነከሩ
ምድራዊውን ትተው ለሰማዩ ኖሩ
ጣዕም ያጣውን ዓለም በቃሉ ለወጡ
እነሱ ጨው ሆነው ሁሉን አጣፈጡ
ምንጭ፦ሐመር ዘኦርቶዶሽ ተዋህዶ
            መስከረም 2009 .

Friday, November 03, 2017

እርቅ ለምኔ

አባቴን በክላሽ እናቴን በርግጫ፣
ወንድሜን በሽጉጥ እህቴን በጡጫ፣
ሲወቃ እያየሁት
ከደጃፌ ጥሎ የበቀል አውድማ፣
በሬየን ቅርጫ አርጎ ሚስቴንም ውሽማ፤
በእናቴ የወጣሁ ሴት መሆኔን አውቆ፣
በወገኖቼ ደም እጁ ተጨማልቆ፤
ህልሙ ሲሞላለት የቅዠቱ ገንቦ፣
ታረቀኝ ይለኛል ዓይኑን በጨው አጥቦ፤
ክንዴን ሳልንተራስ ሳይዝግ ምኒሽሬ፣
መቃብር ሳልወርድ እጅ እግሬን ታስሬ፤
ደመላሽነቴ ሳይታወቅ በዓለም፣
እርቀ ሰላም ብሎ ፍልስፍና የለም።
የወንድሜን ገዳይ ቅንድቡን ሳልመታ፣
የምን ድርድር ነው የምንስ ይቅርታ?

  ©ጌች ቀጭኑ

Thursday, October 19, 2017

ዝጎራ

ረዥም የአማርኛ ጽሑፍ ስታዩ የሚያስነጥሳችሁ ወይም ነስር የሚያስቸግራችሁ ወገኖች ይህንን ጽሑፍ ያለማንበብ ብቻ  ሳይሆን ያለማየት መብታችሁ የተጠበቀ ነው። በእኔ የህይወት ሚዛን ላይ ግን “after many years of struggle now I am your qualified doctor” ብሎ በፖሰቱበት ምሽት ባላገሩ ቢራ ከቅዱስ ጊዮርጊስ፣ በደሌ ከዋሊያ እየቀላቀሉ ሲገለብጡ አምሽቶ፤ እንደ እንክርዳድ ጠላ አፍገምግመው በሚጥሉ ጥያቄዎቻቸው አለማወቃችንን አውቀን እንድናልፍ ያደረጉንን ግለሰቦች ሳይቀር “እከሌ ጮማ፣ እናትህን እንዲህ ላርጋት” እያሉ አስነዋሪ የስድብ ናዳ እያወረዱ ከመግባት ይልቅ ይኸኛው የተሻለ አማራጭ ይመስለኛል።

ከባለ ምጡቅ  አእምሮው ገፀ ባህርይ ጋር ምስጢረኞችን እጽዋት ፍለጋ በሊማሊሞ ገደል  መነሳት መውደቁ፤ እንደ እሳት በሚያቃጥል የጋለ መሬት ላይ በባዶ እግር መጓዙ ። ከእኒያ በፍጹም ስውራኑ እና በክሱታኑ መካከል ያሉ ትልቅ አባት የሚወጡ ነፍስን የሚያለመልሙ ምክሮችን መስማቱ። "ኢትክስት ወኢትንግር ስመ ዝ ጎራ እስመ አኮ መካነ ሁከት ወነጎርጓር ዘእንበለ መካነ ጸሎት ወአርምሞ" የሚለውን ደብዳቤ በፍጹም ተመስጦ ማንበቡ

ፍላጎቱ ያላችሁ ብቻ ታነቡት ዘንድ የምጋብዛችሁ ታሪክ የተፈጸመው ከደብረ ታቦር ከተማ 78ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ ከሚገኝ አንድ ትልቅ ተራራ የበቀለ ደን ውስጥ በሚገኘው ቤተክርስቲያን ነው ።

...ይህን እየተነጋገርን እያለን ግርማ ሞገሳቸው 
የሚያስፈራ 
ረዘም ያሉ አዛውንት መነኩሴ ከወደደኑ አካባቢ ብቅ ሲሉ ሁሉም በአክብሮት ራስቸውን ዝቅ እያደረጉ በመስቀላቸው ተሳለሙ ።የሆነ ብርሃን የከበባቸው ይመስላሉ።አንዳች ነገር ገፋፋኝና ከእግራቸው ስር ወድቅሁ። ትክሻየን ይዘው ቀና አደረጉኝና በመስቀላቸው አሳልመው ግንባሬን ሳም አደረጉኝ ።መላ ሰውነታቸው ዕጣን ዕጣን ይሸታል።

ቢጫ የመናኝ ልብስ ቀኝ እጃቸውን አውጥተው አጣፍተዋል።ከወገባቸው በላይ ትክሻቸው ላይ በከፊል ልብስ አልለበሱም።የፊታቸውና የትክሻቸው ቆዳ ቀለም የቀይ ዳማ የሚባል ሲሆን የፊታቸው ቆዳ ዓይናቸው አካባቢ ከመሸብሸቡ በስተቀር በምቾት የሚኖቱ እንጂ በምናኔ ያሉ አይመስልም።የምንኩስና ቆባቸው በሰሌን ተስርቶ በቆዳ የተለበደ ነው።ከምንኩስና ቆባቸው አምልጦ የወጣው ጥጥ መሳዩ ፀጉራቸው  ከትክሻቸው ላይ እንደሐረግ ተጠማዞ ተኝቷል።የፊታቸው ፂም እንዲሁ ረጅም ሪዝ ሆኖ አንገታቸውን ሸፍኖታል።ደረታቸው ላይ የመባረኪያ መቀል ያንጠለጠሉ ሲሆን ቀኝ እጃቸው ላይ እስከ ክንዳቸው ድረስ ከዕንጨት የተሰራ መቁጠሪያ ተጠምጥሞበታል።በእጃቸው ለአባ መዝገበስላሴ የሰጠሁዋቸውን የዕፆች ቅርንጫፎች ይዘዋቸዋል።የገረመኝ ነገር ግን እኔ ስሰጣቸው እንደጠወልጉት ሳይሆን ፍጹም ለምልመው ነበር።

የፊታቸው ጸዳል የሚለግሱት የትሕትና  ፈገግታ አንዳች መግነጢሳዊ  ሀይል ያለው ቢሆንም ግርማቸው ደግሞ የሸብራል።አባ መዓዛ ቅዱሳን ወደ ጆሮየ ጠጋ ብሎ በለሆሳስ "በፍጹም ስውራኖቹ እና በእኛ መካከል ያሉ አባት ናቸው።በዚህ ወቅት ልታገኝ የምትችለው እኒህን ታላቅ አባት ነው ።የምትፈልገውን መጠየቅ ትችላለህ" አለኝ። ፈዝዤ እንደቆምሁ ፈገግ አሉና "የኔ ልጅ ቃላችንን አክብረህ ትእዛዝችንን በድካምህ ስለፈጸምህ የእግዚአብሔር ፈቃድ ይሁንልህ" አሉና "የሆነው ሆነና ያን ሁሉ ድካም ደክመህ ትእዛዛችን የፈጸምከው ምስጢራችንን ለማወቅ ባለህ ጉጉት ነው ወይስ የዕድሜህ ማጠር አሳስ ቶህ ነው? አሉኝ ።

አባታችን ሞትን የፈራሁት መሰለኝ አልኋቸው "እውነት አለህ የእኔ ልጅ ይሁንና ሞትን ብትፈራውም ብትንቀውም የማይቀር ዕዳ ነው ።የዕድሜህ ማጠር ወይም መርዘም አያስጨንቅህ የፈጣሪ ፈቃድ ነውና ።ይልቁንም በተሰጠችህ እያንዳንዷ ቀን በመልካምና በድስታ ለመኖር ስጋህን ተጠንቀቀው ፣ነፍስህን ቁጠራት፣እምነትህ ን ትሀንቅቀው" አሉና ቀጠሉ።እኔ ብቻ ሳልሆን ሁሉም በተመስጦ እያዳማጡ ነበር። "ኢትዮጵያዊነት በ አምስት አምዶች የታነጸ መኖሪያ እልፍኝ ነው ።ጥልቅና ሰፊ እውቀት ፣መዛል የሌለበት ትጋት፣በትዕግስት የታሸ ጀግንነት ፣ርኩሰት የሌለበት ቅድስና፣ግብዝነት የሌለበት ምስጢራዊ ህይወት ነው።"

"የምስጢር ሙዳይ ሁን እንጅ የእሳት ማንደጃ ወናፍ አትሁን ።ሰዎች ሊሰሙህ በሚችሉት ችሎታቸውና ፍላጎታቸው መጠን ብቻ ተናገር ፣ቁጥብ እንጂ ዝርው አትሁን ።ለእውቀት ትጋ።በከፊል በተረዳሃው ነገር ራስህን እንደ አዋቂ አትቁጠር ።በከፊል ከማወቅ አለማወቅ ይሻላል።ስራ ስትሰራ ደግሞ ነገ ትቼው ለምሞተው ወይም ብሰራ የሚጠቀመው ሌላ ነው በሚል ተስፋ ቢስ ሆነህ ሳይሆን ዘላለም እንደምትኖር
ክል በመትጋት ነው ።ትጋት ጥሩ ነው ።ችኮላህ ግን ውጤት አያመጣም፣በችኮላ መስራትና በፍጥነት መስራት የተለያዩ ናቸው ።ርኩሰት የዕውቀትና የስልጣኔ መገለጫ አይደለምና ማንነትንና ሰብዓዊ ክብርን ከሚያጎድፉ ተግባራት መታቀብን ገንዘብ አድርግ።

እናም በእየ ዕለቱ በኑሮህ ጠንቃቃ ሁን ።ያለጸጸት ነገን ለመኖር ዛሬን በቁም ነገር አሳልፍ።ውሳኔዎጭችህን መርምር፣ልክ እንደገና ህይወትን የመኖር ዕድል ቢኖርህ ደግመህ የምትኖረውንና ለማከናወን የምትመርጠውን ዐይነት ህይወት ለመኖር ሞክር ።እንዲህ ያለ ጥያቀ ብትጠየቅ ምልስህ ምንድን ይሆን? እንደገና የመወለድ ምርጫ ቢኖርህ ኢትዮጵያ ውስጥ ኢትዮጵያዊ ሆነህ ለመውለድ ትመርጣለውህ? የያዝከውንስ ሙያ በድጋሜ ትመርጠዋለህን? ያገባሃትን ሚስትስ እንደገና ታገባታለህ? ወይስ መነኩሴ ከሆንህ እንደገና የምንኩስና ህይወትን ትደግመዋለህን?" አሉና እፆቹን ወደ አፍንጫቸው አስጠግተው እንደ ማሽተት አደርጉ።

"ዕፁን ለምን እንድታመጣ እንደፈለግን ብርቱ ምስጢር ነውና  ወንድምህ አባ መዓዛ ቅዱሳን ወደፊት ይነግርሃልና በልብህ ጠብቀው።በእምነትህና በትጋትህ ልክ የስራ ድርሻ ይኖርሃል።ፈ
ሪ ምህረቱንና ጸጋውን ያብዛልህ ።ወላዲተ አምላክ አትለይህ።"ብለው ትክሻየ ላይ በግራ ዕጃቸው  ማጣፊያ ስር ይዘውት የነበረውን ምርኩዛቸውን በቀስታ ል ሲያደርጉብኝ በቀስታ ልቤን ጉትት አድርጎ ሲወስደኛና ራሴን ለመሳት ሲከጅለኝ ታወቅኝ።ዐይኖቼ የቀስተደመና ቀለማትን ከደኑ ላይ  የሚያዩ መስለኝ።ምን ያክል ሰዓት እንደቆየሁ አላውቅም ደስ የሚል የሰላም እንቅልፍ ወስዶት እንደቆየ ሰው ከድካምና ከቁስል ጥዝጣዜ ስሜት ነፃ ሆኜ ተነሳሁ።



ምንጭ፦ዝጎራ በአለማየሁ ዋሴ እሸቴ


Sunday, October 15, 2017

ታላቅ የምስራች

ታላቅ  የምስራች ለደስታዬ ተካፋዮች በሙሉ እነሆ ያኔ ገና  በልጅነት እድሜ በግ እና ፍየሎችን እየጠበቅሁ ያኸለምሁት ህልሜ  እውን መሆኑን  ምክንያት በማድረግ ከዛሬ ጀምሮ ብሸከም የማልችለውን  ማዕረግ ከፊት በማስቀደም ዶ/ር  ጌታነህ ካሴ ተብዬ እንድጠራ የተፈቀደልኝ መሆኑን ስገልጽላችሁ በታላቅ ደስታ  ነው። ዘወትር  ከጎኔ ሁናችሁ አይዞህ እያላችሁ ለዚህ ታላቅ ክብር እንድበቃ ላደረጋችሁኝ ወንድሞቼና እህቶቼ በሙሉ ውለታችሁን ከፍየ አልጨርሰውምና  እግዚአብሔር ዋጋችሁን  እጥፍ ድርብ አድርጎ ይክፈላችሁ  እላለሁ። እውነት ለመናገር በዚህ ሰው አምላኩን ረስቶ  ገንዘቡን ማምለክ በጀመረበት ዘመን “መወለድ ቋንቋ ነው” የሚለውን ብሂል በተግባር ያሳያችሁኝ ለእኔ የተሰራችሁ የፍቅር ጣኦታት  ናችሁና ሳመሰግናችሁ ውየ ሳመሰግናችሁ ባድር አይወጣልኝም። ተምሮ ሰው ይሆንልኛል በሚል ተስፋ ከእለት ጉርሳችሁ ይልቅ ለእኔ በማድላት ላስተማራችሁኝና ጠንቅራችሁ ብርታት ለሆናችሁኝ ቤተሰቦቼ ደስ ብሎኛልና ደስ ይበላችሁ እላለሁ። በቸርነቱ ብዛት ለዚህ ያበቃኝ አምላክ ከእናቱና ከቅዱሳኑ  ሁሉ ጋር ክብርና ምስጋና ይድረሰው። አቤቱ የሰራዊት ጌታ እግዚአብሔር ሆይ  የልመናየን ቃል ሰምተኸኛል እና  አመሰግንሃለሁ። ድንግል ሆይ አንቺ የጽርሐዓርያም ብርሃን ከጎኔ ሆነሽ ታረጋጊኝና ግርማ ሞገሥ ትሆኝኝ ዘንድ እኔ ማን ነኝ
      መች ተነግሮ ያልቃል ያምላክ ቸርነቱ
እኛስ ብለን ነበር ቀረን ሆነን ከንቱ
በፍፁም ትሕትና አሃዱ ቢል ቄሱ
በመልካም ውብ ዜማ ስሉስ ቢቀደሱ
መንቨሩ ፊት  ብትቆም ደጓ የዓለም ቤዛ
አምላክም በፋንታው ምህረቱን  አበዛ
በሃያል ስልጣኑ ጥልን  ደመሰሰ
ያጣነው ልጅነት ዳግም ተመለሰ
መለያየት  ቀረ ውላችን ታደሰ
እረኞች ዘመሩ ፍጥረት ተደመመ
በህይወት  አዳራሽ  ማህሌት ተቆመ
Dr. Getaneh Kassie

Thursday, September 21, 2017

እጃችን አንሰጥም

ሂትለር ቢያንገራግር ጎልያድ ቢዝትም፣
አልመን ባንመታ ተኩሰን ብንስትም፣
ወንጭፍ ሳይበጠስ እጃችን አንሰጥም።
ከማር ሸክም ሲበልጥ የቴንሽን ሚዛኑ፣
“ደሞዝ ተጨምሯል”ብላችሁ ተጽናኑ።

Saturday, September 02, 2017

እስኪ ይጠየቁ

ወደታች ስንት ነው የባህር ጥልቀቱ?
ዓለምስ ወደጎን ስንት ነው ስፋቱ?
መሬትና  ፀሐይ ስንት ይራራቃሉ?
የሰማይ ከዋከብት  እንዴት ይደምቃሉ?
የሲዖል ጨለማ  ምን ያህል ይጠልቃል?
የሰው ልጅ ልቦና  ምን  ያህል ይመጥቃል?
አእምሮ ቢጠበብ እስከ የት ጥግ ያውቃል?
ሁሉም ወሰን አለው አብጅቷል ዳር ድንበር፣
ፍፁም አይደለችም ደምቃ  አትቀርም ጀንበር።
ሁሉም ጎደሎ ነው ይሻል ሌላ ግባት ፣
ትዕግስት ጠረፍ አለው ገደብ አለው ጽናት
ምኗም ሙሉ አይደለም ዓለምም ባዶ ናት፤
ቀንም ያለ ፀሐይ ሌት ያለ ጨረቃ፣
አቅም የላቸውም ድኩም ናቸው በቃ።
አድሮ ይቀየራል ሰው ወረተኛ ነው፣
ውዱን ያሞካሻል ነገ ሊኮንነው።
ፍጥረት ግፈኛ ነው እራሱን ይወዳል፣
ህሊናውን ክዶ ጥቅሙን ያሳድዳል።
እስከማላውቀው ጥግ የሚወድሽ ሆዴ፣
ታዲያ እኔ ምንድን ነኝ ሰው አይደለሁ እንዴ?
በማዕረግ ብመረቅ ብሆን  ተሸላሚ፣
ሪከርድ  በመስበር ሰውን አስደማሚ፣
ፍጥረት የሚያደንቀኝ ብሆን የሰው ጀግና፣
ትንሹም  ትልቁም የሚያውቀኝ በዝና ፤
ተሸናፊም ብሆን ምስኪን የሰው ተራ ፣
ከአስጨብጫቢዎች ጋር ስሜ ማይጠራ፣
ተገፍቸም ብወድቅ ይች ዓለም ብትክደኝ፣
ከምወድሽ በላይ ልብሽ የሚወደኝ፤
ምኞት ምርቃትሽ የሆነኝ መከታ፣
ቁጣና እርግማንሽ በማይበረታ
እስኪ መልሽልኝ ልጠይቅሽ  ለአፍታ፤
ሳይበሉ የሚያጠግብ ስምሽን ሲጠሩ፣
ወሰን አልባው ፍቅርሽ  ምንድነው ምስጢሩ?
ሲያስቡሽ ፈገግታን ደስታን የምትሰጭ፣
በቀዝቃዛ ዓለም ውስጥ ሙቀት የምትረጭ፤
ውለታ ማትቆጥሪ ወረት የማታውቂ
ስለ አብራክሽ ክፋይ የምትጨነቂ፤
ድህነት ቢይዘው እጅሽን ጨምድዶ፣
ገላሽ በጋሬጣ እንደ ፍየል ታርዶ፣
የማይታጠፍ ክንድ ተንቆም ተዋርዶ፤
የማይደክም ወገብ የማይዝል ትክሻ፣
አቅፎ የሚደግፍ እስመ መጨረሻ ፤
የደፈረሱ ዓይኖች በጭስ የጠገጉ፣
ሸካራ መዳፎች በእሾህ የተወጉ፤
ጎስቋላ ግርባቶች ጫማ የማያውቁ፣
ሰንጣቃ ከናፍርት በብርድ የደረቁ፣
እስኪ ቢፈቅዱልኝ ዛሬስ ይጠየቁ።
ጥግ የሌለው ጽናት ተስፋው ያልተነካ
ልጅሽ የማይመስልሽ በልቶ የሚረካ ፤
ለእርሱ የተኖረ የእድሜሽ እኩሌታ፣
ሁሌም በመጨነቅ  ዘወትር ጧት ማታ፤
ሊገልፅ የማይችለው የብዕሬ ጠብታ፣
ትርጓሜው ምንድን ነው የፍቅርሽ አንድምታ?
አፍሽን ክፈችው እስኪ እንነጋገር፣
ወረት የማይገዛሽ ባትሆኝ ገራገር፣
ለውለታሽ ምላሽ ምን ይከፈል ነበር?
©ጌች ቀጭኑ: ለእናቴ ወ/ሮ ትሁኔ ዋሴ
                   ነሐሴ 27/2009 .

Thursday, August 17, 2017

ሳይኮፓትስ

ለጋራ ደህንነት የማይጨነቁ
ጤነኛ ነን ሲሉ ታመው የማቀቁ
ላያቸው  ያማረ  ልስን መቃብሮች
በበግ ለምድ ያጌጡ አስመሳይ ቀበሮች
አጉራ ዘለል ወይፈን ተራጋጭ ጊደሮች
ጋውን የለበሱ የተቋም አውሬዎች
ጊዜ ያለፈበት ክኒን ቸርቻሪዎች
ከአምላክ የተጣሉ አሉ ወንበዴዎች
ሐኪሞች ሲባሉ የመርዝ ነጋዴዎች
ባለጌ መች አጣን አሉን ጋጠ ወጦች
በልተው የማይጠግቡ የሆስፒታል አይጦች
መርዛቸው  የማይለቅ ተናዳፊ ጊንጦች
ወንጀል በዞረበት ቦታ ማይታጡ
እጅ ከፍንጅ ተይዘው የማይደነግጡ
ላደጉበት ባህል እውቅና ማይሰጡ
ለምድራዊ ሥልጣን የማይታዘዙ
ለፈጣሪያቸው ህግ ፍጹም ማይገዙ
በዓይነ ስውር ፎቶ ዶላር ሚበደሩ
የድሃ አደጉን ልጅ ጾም የሚያሳድሩ
ከረዥም ልምዳቸው እውቀት ማይቀምሩ
አሊያም ከደጋጎች አንዳች ማይማሩ
በዝባዦች ሞልተዋል በየጉራንጉሩ
ውስጣቸው ሲገለጥ እጅግ ሚከረፉ
ከአጋንንት አለቆች በግብር የከፉ
ከሙዳዬ ምፅዋት ቅኔ የሚዘርፉ
ደግ ቅን አሳቢ ጤነኛ ሚመስሉ
አትሮኖስ ላይ ቆመው መንፈስ ሚያታልሉ
መዝሙር ሲያልቅባቸው ቀረርቶ ሚሞሉ
በበትረ ሙሴ አምሳል ለአንገት ሰይፍ ሚስሉ
ከቤተ መንግስትም ከቤተ መቅደስም ሳይኮፓቶች አሉ


Note: Psychopaths are individuals with Antisocial personality disorder and they are characterized by Continuous disregard for the safety of oneself and others, Violation of the rights of others without feeling remorse, Failure to learn from experience, Social deviance, Manipulative or parasitic attitude and Resistance to authorities. They often wear ‘a mask of sanity' and may appear quite normal, charming, and understanding. Surprisingly there are three and half times more psychopaths in senior executive positions than there are in the general population.
©ጌች ቀጭኑ ነሐሴ 11/2009 ዓ.

Tuesday, August 08, 2017

እይታ

ከሁሉ አስቀድሜ በዚች አጭር ጽሑፍ ቢሆን ጥሩ ነው ብዬ የማስበውን ሀሳብ ለማስተላለፍ  እንጅ አንዱን አሳንሶ ሌላውን ከፍ የማድረግ ዓላማ እንደሌለኝ ለመግለጽ እወዳለሁ። ምናልባት መስሎ የሚታየው ካለ ግን እርሱ አስተሳስቡን ያስተካክል።

ያ ስሙን የማላስታውሰው መዝገበ ቃላት “ስብሰባ የሚለው ቃል በቁሙ ሲፈታ  ውኃ ውኃ የሚሉ ሰዎች ተመራርጠው የሚሰባሰቡበት፤ በየደቂቃው አፋቸውን በሀይላንድ ውኃ እየተጉመጣመጡ ውኃ የማያነሳ ሀሳባቸውን የሚሰነዝሩበት ፤ በመጨረሻም ከውኃ የቀጠነ ውሳኔ አሳልፈው የሚለያዩበት የሰዎች ጥርቅም ነው ” ያለው እውነቱን ሳይሆን አልቀረም። እንደዚህ የምለው ያለ ምክንያት አይደለም፤ ላለፉት አራት ዓመታት እንዳስተዋልሁት  ክረምት  በመጣ ቁጥር ለዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች እየተባለ የተለያዩ ስብሰባዎች (ስልጠናዎች)ተዘጋጅተዋል ተካሂደዋልም። አንዳቸውም ግን የህክምና ተማሪዎችን  አሳትፈው አያውቁም ። ከ“ጥልቅ ተሐድሶ”ው በስተቀር።

“ይህ የሆነው የህክምና ተማሪዎች ጊዜ ስሌላቸው ነው።” ብሎ የሚከራከር የዋህ ይኖር ይሆናል። እኔ ግን አይመስለኝም። የስብሰባው አስፈላጊነት ከታመነበት በስብሰባው መሳተፍ ያለባቸው ጊዜ ተትረፍርፎባቸው “ክረምቱን በምን እናሳልፈው” የሚሉት ሳይሆኑ ጊዚያቸውን አጣበው የሚጠቀሙት ናቸው። ምክንያቱም በትርፍ ጊዜው የሚሰበሰብ ሰው ሃሳብ  የሚሰጠውም  ውሳኔ  የሚወስነውም ትርፍ ጊዜ  ስላለው እንጅ አስፈላጊነቱን አምኖበትና ከልቡ አስቦበት ነው ለማለት ይከብደኛል።

በመሰረቱ ለአንዲት ሀገር እድገት የሚያስፈልገው ሥራ ነው እንጅ ስብሰባ ነው ብዬ አላምንም። የግድ ስብሰባ ያስፈልጋል ከተባለ ግን  በ12ኛ ክፍል ፈተና የተሻለ ውጤት አስመዝግበው ህክምና  ትምህርት ቤት የገቡ ተማሪዎችን ማሳተፍ አማራጭ የሌለው ግዴታ ይመስለኛል።“ከተባለ ወዲያ እናርገው በፍቅር ጥርስዎን ያውሱኝ ድንቸ ቆሞ አይቅር” እንዲሉ አያቴ ። እውነት ችግሩ የጊዜ ማነስ ከሆነ ሁለት ሳምንት የሚፈጀውን ስልጠና አጠር መጠን አድርጎ በአራት ወይም በአምስ ቀናት መጨረስ  ያማይቻል ሆኖ ነው? ከህክምና ተማሪ ጭንቅላት የሚመነጨውን ሃሳብ መረዳት የሚችል፣ የሚጠይቁትንም   ጥያቄ የመመልስ አቅሙ ያለው የስብሰባ መሪ ከተገኘ ማለቴ ነው።

መቼም እየተደረገ እንዳለው የAnesthesia ተማሪዎች የ”medicine” ተማሪዎችን ወክለው ይወስኑ ብሎ የሚሟገት ይኖራል ብዬ አላስብም።

©ጌች ቀጭኑ ነሐሴ 2/2009 .

Saturday, August 05, 2017

ችግር ሲደራርብ

አንዳንዴ  ችግሮች ሁሉ በሰው ላይ ያድማሉ። የመጀመሪያው ችግር ያስከተለው ሃዘንና መከራ ከልብ ሳጠፋ ሁለተኛው ይከተላል። መከራ መከራን እየመዘዘ በመሳሳብ የተቀባዩን  አሳርና ፍዳ ያበዛዋል። ጊዜና ምክንያት ተረዳድተው የችግር ሰንሰለት፣የመከራ ቀለበት  ይፈጥራሉ። በሰንሰለቱ የታሰረ በቀለበቱ የታጠረ እዬዬን ዘፈኑ አድርጎ ብሶትና ትካዜን ሲያንጎራጉር ተስፋ ቆርጦ ተስፋን  እያበቀለ ጊዜ ያመጣበትን  ጊዜ እስኪያስረሳው አካል መንፈሱ ይንገላታል። አንዳንዱ ሃዘንና ችግሩን አፍ አውጥቶ ለሌላው በማካፈል አልቅሶ ይለቀስለታል፤አዝኖ ይታዘንለታል። ያም ብቻ ሳይሆን ከከንፈር መምጠጥ አንስቶ እስከ ከባድና ውስብስብ ደረጃ ያለ እርዳታና መፍትሄ ሁሉ ይለገሰዋል። እናም ትንሽ ሲነካ ብዙ በመጮህ ችግሩ ሳይጎዳው በፊት የቅርብ የሩቅ ወዳጁን አስቸግሮ በእንጭጩ ይቀጨዋል። አንዳንዱ ደግሞ ለዚህ አልታደለም። ችግሩን ለብቻው አፍኖ በመያዝ ወደ ውስጡ እያነባ መንፈሱን በጭነንቀት እያደቀቀ አካሉን በጥያቄ እስኪያስገምት ይብሰከሰካል። ብዙ ጊዜ ሐሳብና ችግራቸውን ለብቻቸው ይዘው የሚብሰለሰሉ ሰዎች አካባቢያቸውን በስጋት የሚመለከቱ ናቸው ። ፍርሃትና ጥርጣሬ አይለያቸውም ። እምነታቸው በራሳቸው ላይ ብቻ በመሆኑም ችግራቸውን በውስጣቸው አምቀው በይሉኝታ፣በእልህና በመግደርደር  አጽናኝ ረዳት ሳያገኙ ጉዳታቸው እያየለና እየከፋ በመሄድ በእነሱ ፍላጎት ሳይሆን በችግራቸው ከአቅም በላይ መሆን ይጋለጣሉ። ነገር ግን ከረፈደ ነውና ከዘመድ ወዳጅ ሊያገኙ የሚችሉት እርዳታ ችግራቸው የሚወገድበትን ሳይሆን ችግራቸውን አምነው የሚቀበሉበትን ምክርና መፍትሔ ነው። ይህ ጽሑፍ ገመና የተሰኘ ረዥም ልብወለድ ሳነብ ያገኘሁትና በማስታወሻ ደብተሬ ከትቤ ያስቀመጥሁት ሲሆን በዛሬው እለት አንዲት የፌስቡክ ጓደኛዬ “ዛሬ ባጣም ክፍት ብሎኛል“ ብላ ፖስት ስታደርግ ከጠቀማት ብዬ ልኬላት በጣም እንደወደደችው ስለገለጸችልኝ በጦማሬ ላይ ላሰፍረው ተገድጃለሁ።ጥሎብኝ ሴት ልጅ ስትከፋ ማዬት አልወድም።
 ያለ ጭንቅ አይወጣም የሴት ልጅ ገንዘቧ፣
በከፈለች ማግስት ይቀጥናል ወገቧ፤
እያልሁኝ እሟገት እከራከር ነበር፣
መሆኗ ሳይገባኝ የልግስና በር።
ጌች ቀጭኑ!

Friday, August 04, 2017

እንጨት ሽበት

በስቴቶስኮፑ ላይ  ዝናውን ደርቦ፣
ዶክተሩ ብቅ ሲል ስድብን ተርቦ፣
ነጭ ላብ  ሲያመነጭ ተሜ ከግንባሩ፣
ዋርዱም ይጨነቃል ይቆማል ባንድ እግሩ።
አሁን በቀደምለት !
ምሁር ከኔ በላይ አዋቂነት ላሳር፣
ነው ብሎ የሚያምን ከንቱ ነው ስንክሳር፤
ዝም በል አትንጣጣ እንደ ተልባ ቆሎ፣
ስትጠየቅ ብቻ መልስ ስጥ በቶሎ።
በሽታውን ካወቅህ መድኃኒቱን አምጣ፣
የማትችል ከሆነ አማራጭ ምታጣ፣
በመስኮት  ልጣልህ ወይም በበር ውጣ፣
አንች ደግሞ ዝፍዝፍ ምን ተዘርግፈሻል፣
ስታጨሽ ስትቅሚ ቀን ነግቶ ይመሻል፤
ሀገርሽ ወዴት ነው ትመስያለሽ ጭቁን፣
ለካስ ወሎዬ ነሽ የተቋቋምሽ ድርቁን።
አንተን ደግሞ አለት ራስ ተስፋህ የጨለመ፣
አስተምሮ ሰው ሊያረግ ማን ለምን  አለመ?
አድረህ ላትሻሻል በከንቱ ደከመ።
ገዳይ የለም እንጅ ሟችማ መች ጠፋ፣
ድንቁርናም በዛ ባዶነት ተስፋፋ።
እያለ ሲዘልፈን ሲሰድበን ሲቆጣን፣
ቁም ቅምጥ ሲነሳ መድረሻ ሲያሳጣን፤
አባቱን ሊጠይቅ የመጣ አንድ ጎልማሳ፣
እንዲህ ሲል ተቀኘ ብዕሩን አነሳ፣
አወይ እንጨት ሽበት አጉል ሽምግልና፣
ለማንም የማይበጅ ከንቱ ፍልስፍና፣
ጥበብ በፀጋ እንጅ መች በእድሜ ሆነና።

ጌች ቀጭኑ ከ“ward” መልስ ሐምሌ 25/2009 .

Monday, July 24, 2017

የሐበሻ ቀጠሮ

የሐበሻ ቀጠሮ ሲባል ግን አይገርማችሁም? በፈረንጅኛ እንማራለን በፈረንጅኛ እናስተምራለን፣በፈረንጅኛ እንታመማለን፣ በፈረንጅኛ ታክመን በፈረንጅኛ እንድናለን። በፈረንጅኛ እንመርቃለን(እናመሰግናለን)፣በፈረንጅኛ እንሳደባለን። በቢዮንሴ እና በሻኪራ ዘፈን እንጨፍራለን፤ የፈረንጅ ልብስ እንለብሳለን፤ የፈረንጅ መጠጥ እንጠጣለን፤የፈረንጅ ምግብ እንመገባለን (ለማለት ቢከብድም)። ከፈረንጅ ያልወረስነው ነገር ምን አለ? እንደ እኔ ከፈረንጅ ያልኮረጅነው ነገር ቢኖር የቀጠሮ አከባበራቸውን ብቻ ነው። ፈረንጆች የሚሆኑትን ሁሉ እንሆናለን። የሚያደርጉትንም እንደ አቅማችን ለማድረግ እንጥራለን። የሰዓት አጠቃቀማቸውን ለመስረቅ ሙከራ ሲያደርግ የተያዘ ወንጀለኛ ግን ያለ አይመስለኝም።ይልቁንም ደካማ የጊዜ አጠቃቀማችንን የሐበሻ ቀጠሮ የሚል ሽፋን እንሰጠዋለን።

የሐበሻ ቀሚስ ከተነደፈ ጥጥ ይሸመን ከታኘከ ማስቲካ ይሰራ የማያውቁት ሴቶቻችን እንኳን ዳሌያቸውን ከጉልበቱ ላይ በተቀደደ የቻይና ጅንስ ወጥረው ለምን የቀጠሮ ሰዓት እንዳላከበሩ ሲጠየቁ “ምን ይደረግ የሐበሻ ቀጠሮ አይደል” ማለት ይቀናቸዋል። ወይ ሐበሻ እቴ ድንቄም ሀበሻ! የማር ሰፈፍ የመሰለ እንጀራ ጋገሮና በቅምጥ የሚስቀር ጠላ ጠምቆ ነበር እንጅ ሐበሻነትን ማስመስከር። “ትርክርክ” አለች አክስቴ። በነገራችን ላይ እኔ እስከማድግ ድረስ ሴቶቻችን በዚህ ከቀጠሉና ለቀጠሮ ያላቸው አመለካከት ካልተስተካከለ ቆሞ ቀር እባላለሁ እንጅ ሚስት የምትባል ጉድ ላለማግባት ቁርጥ ያለ ውሳኔ ላይ ደርሻለሁ። በቃ አዱኛ አበባዬን ሳላይ ብሞት ይሻለኛል።(የመጀመሪያ ሚስቴን ልፈታት ስላሰብሁ ከተሳከልኝ ማለቴ ነው) ። ቀጠሮ የማታከብር ሴት ቱ... ሞቻለኋ!

ምን ለማለት ፈልጌ ነበር ? ባለፈው ቅዳሜ እለት የሆነች ስልጠና ቢጤ ለመሳተፍ ከጥዋቱ 2:00 ላይ የሆነ ቦታ ተገኝቸ ነበር። ስልጠናው ወይም ስብሰባው በማስታወቂያ ከተገለፀው ሰዓት 80 ደቂቃዎችን ብቻ ዘግይቶ ተጀመረ። ወደ ስብሰባው አዳራሽ በጓሮ በር ገብተን እንደተቀመጥን ግማሽ ሌትር የሀይላድ ውኃ በነፍስ ወከፍ ታደለን። (እኔም እንደሰው ወግ ደርሶኝ የሀይላንድ ውኃ እየጠጣሁ ስብሰባ ስሳተፍ ይህ የመጀመሪዬ ነው። ከነ እማማ ደብሬ ቤት በታች ካለችው ቤተመጽሐፍት ውስጥ የሚገኝ አንድ ስሙን የማላስታውሰው መዝገበ ቃላት “ስብሰባ የሚለው ቃል በቁሙ ሲፈታ ውኃ ውኃ የሚሉ ሰዎች ተመራርጠው የሚሰባሰቡበት፤ በየደቂቃው አፋቸውን በሀይላንድ ውኃ እየተጉመጣመጡ ውኃ የማያነሳ ሀሳባቸውን የሚሰነዝሩበት ፤ በመጨረሻም ከውኃ የቀጠነ ውሳኔ አሳልፈው የሚለያዩበት የሰዎች ጥርቅም ነው ”ይላል።)

ወደ ቀደመ ነገራችን እንመለስ በተሰጠችኝ ውኃ ንዴቴን አብርጄ አገር ሰላም ብዬ በተቀመጥሁበት ከመርሀግብር መሪዎቹ አንዷ ወደመድረክ ሰበር ሰካ እያለች ወጣችና ቀብረር ብላ “good morning every body welcome to …”አለች በፈረንጅኛ ነው እኮ። አቅለሸለሸኝ ጨጓራዬ ተነሳብኝ፤ በቃ ተቃጠልሁ። ሊነስረኝም አማረው። አሁንም ቀጠለች “….. let’s have some ground rules… first thing is punctuality. Punctuality or timely arrival is a must .” ብላን እርፍ።መቼስ ሰማንያ ደቂቃ አርፍዶ የመጣ ሰው ሰዓት አክባሪ ለመምሰል ሲገዳደር ያልወረደ መብረቅ እራሱም ዘገምተኛ መሆን አለበት።

እንዴው ፈጣሪ አያድርግብኝና የሰይጣን ጆሮም አይሳማ እንጂ ሰሞኑን የጨጓራ በሽታዬ ድጋሜ ከተነሳ ምክንያቱ ከወ.መ.ሽ ሰልፍ እና ቀጠሮ ከማያከብሩ ሰዎች የዘለለ አይሆንም። አይ ወመሽ ወመሽ እኮ ሰልፍ ይወዳል። ካፌ ሰልፍ፣ ሻይ ቤት ሰልፍ፣ ቡና ቤት ሰልፍ፣ ሽንት ቤት ሰልፍ ፣ ሰልፍ ፣ ሰልፍ፣ ሰልፍ ነው ።

Wednesday, July 19, 2017

እርሳኝ አትበይኝ

በድል ያሳለፍሽኝ የሞትን አደጋ፣
እንዳይ የረዳሽኝ የህይወትን ዋጋ፣
የልፋት ደሞዜን የተጋድሎን ፀጋ፤
በውለታሽ ብዛት ያረግሽኝ ባለዳ፣
የመስከረም አደይ ውቧ ጽጌረዳ ፣
ልቤን ያሸፈትሽው ገና በማለዳ፤
ፍቅርን የሰጠሽኝ ጠቅልለሽ በሸማ፣
ስምሽ በአንደበቴ ከፍ የሚል ከማማ፤
ከእንቅልፍ የሚያነቃኝ የጉርሻሽ ትዝታ፣
ድምጽሽ ሚያባንነኝ ሁሌም ጥዋት ማታ፤
ከብርንዶ ይልቅ ሽሮሽ ሚናፍቀኝ፣
አንች በሌለሽበት ወለላ የሚያንቀኝ፤
ተዳፍነሽ የቀረረሽ የልቤን ውስጥ እሳት ፣
እንዴት ይቻለኛል እኔ አንቺን ለመርሳት?
አበባ ጥርሶችሽ ከኔ ይሰንብቱ፣
ሳቅና ጨዋታ ዝና የሚያውቁቱ፤
ብዬ ያዜምሁልሽ የሀሴት ዝማሬ፣
በናፍቆትሽ ብርታት ስባዝን አድሬ፤
አምባገነን ሥልጣን ከላይ የተቸረው ፣
መተተኛ ዲያቆን አንደበቴን  ቢያስረው፤
ማሰንበት ቢቻለው ጭድን ከእሳት ጋራ፣
ማስታረቅ ቢያውቅበት ሸማን ከገሞራ፣
በአንቺ እና እኔ መሀል ቢያፈልስ ተራራ፣
መውደዴን ባልነግርሽ ቢያዝ አንደበቴ፣
እርሳኝ አትበይኝ አይችልም አንጀቴ።
ፍቅሬን ባልገልጽልሽ ቢዘጋ ልሳኔ፣
እርሳኝ አትበይኝ ችሎ አይችልም ጎኔ።

©ጌች ቀጭኑ ለY.F ሐምሌ 12/2009 .

Thursday, July 13, 2017

ማን ዘርቶ ማን ያጭዳል?

አንድ አርሶ አደር  ያልዘራውን ስንዴ ወይም አርሞ ኮትኩቶ ያላሳደገውን አዝመራ መከር ሲደርስ እሰበስባለሁ ብሎ ሊከራከር እንደማይችል ማንም ሰው የሚያውቀው ጉዳይ ይመስለኛል። ታዲያ  በዩኒቨርሲቲ ቆይታው ተቸጋግሮ  ሲማር፣ እንደ አጋጣሚ በንባብ ተጠምዶ ሳያስበው የካፌ ሰዓት በማለፉ ጾሙን ድፍት ብሎ ሲያድር፣ እንደ ሌሎች ሻይ ቡና ብሎ ወደ ንባብ የሚመለስበትን ቀን ሲናፍቅ፣ ይቺ የሻይ ቡና ይቺ ደግሞ የሳሙና  ትሁንህ ያላሉትን ተማሪ ዛሬ ላይ ዳቦ ጋግሬ፣ ጠላ ጠምቄ፣ ሙክት አርጄ፣ ፍሪዳ ጥዬ አስመርቅሀለሁ ማለት የሞላኝ የደላኝ ሀብታም ነኝ ብሎ ለመመፃደቅ ካልሆነ በቀር ሌላ  ምን ትርጉም ይኖረዋል? ተቀያሪ በሌላቸው ልብሶቹ የጓደኞቹ መሳለቂያ  እስከሚሆን ሲቸገር  ለደብተር እና ለእስክርቢቶ እጁን ያልዘረጋ ዘመድ የምረቃ ዕለት እንደ ድንገት የ90 ብር አበባ እና የ5ሺህ ብር ስማርትፎን ይዞ ማዘጥዘጡስ ምን ሊበጅ? ማን የዘራውን፣ ማን አርሞና ኮትኩቶ  ያሳደገውን፣ ማን ያጭዳልያልዘሩትን አጫጅ ከመሆን ይሰውረንማ አቮ !!! ለማንኛውም ተመራቂዎች እንኳን ደስ ያላችሁ ብያለሁ።
 ሰኔ 1/2009 .ም :ሲስኮ

Tuesday, July 11, 2017

አታሳደኝ በለኝ


ወደህና ፈቅደህ የፈጠርኸኝ ጌታ፣

ምስጋና ይብዛልህ ይድረስህ ሰላምታ።

በመላእክት ሀገር በጻድቃን ከተማ፣

ክብርህ የገነነ በኤረር በራማ፣

ጸሎቴን ተቀበል ልመናዬን ስማ።

ማሳደጃ ጦማር የሹመት ደብዳቤ፣

የሀጢአት ፍላጻን በወገቤ አንግቤ፣

በዝሙት በሐሜት በክፋት ታጅቤ፣

ወንጌል ዲቃላ ስል ጥበብን ተርቤ፤

የመወጊያውን ብረት ስቃወም በፀና፣

“አታሳደኝ” በለኝ ድምጽን አሰማና።

በምድረ ደማስቆ የወረደው መብረቅ፣

የልቤን ደጅ ይምታ አለቱም ይሰንጠቅ፤

ሳታቆስል ማርከኝ አድርገኝ ምርጥ እቃ፣

ስምህ በአንደበቴ የሞተ ሰው ያንቃ።

የእስር ቤቱ መዝጊያ መሀሉ ይፈለጥ፣

ክብርና ሞገስህን በባሪያህ ላይ ግለጥ።

በደስታ ልዘምር ምድር ትደባለቅ፣

ጠላቴን ይጭነቀው አካላቱ ይለቅ።

ጸናጽሌን ልያዝ ከበሮዬን  ልምታ፣

ዓለም ግሩም ትበል ታምርህን አይታ።

((©ጌች ቀጭኑ)):ገዳም ሰፈር
ሐምሌ 4/2009 ዓ.