Tuesday, July 11, 2017

አታሳደኝ በለኝ


ወደህና ፈቅደህ የፈጠርኸኝ ጌታ፣

ምስጋና ይብዛልህ ይድረስህ ሰላምታ።

በመላእክት ሀገር በጻድቃን ከተማ፣

ክብርህ የገነነ በኤረር በራማ፣

ጸሎቴን ተቀበል ልመናዬን ስማ።

ማሳደጃ ጦማር የሹመት ደብዳቤ፣

የሀጢአት ፍላጻን በወገቤ አንግቤ፣

በዝሙት በሐሜት በክፋት ታጅቤ፣

ወንጌል ዲቃላ ስል ጥበብን ተርቤ፤

የመወጊያውን ብረት ስቃወም በፀና፣

“አታሳደኝ” በለኝ ድምጽን አሰማና።

በምድረ ደማስቆ የወረደው መብረቅ፣

የልቤን ደጅ ይምታ አለቱም ይሰንጠቅ፤

ሳታቆስል ማርከኝ አድርገኝ ምርጥ እቃ፣

ስምህ በአንደበቴ የሞተ ሰው ያንቃ።

የእስር ቤቱ መዝጊያ መሀሉ ይፈለጥ፣

ክብርና ሞገስህን በባሪያህ ላይ ግለጥ።

በደስታ ልዘምር ምድር ትደባለቅ፣

ጠላቴን ይጭነቀው አካላቱ ይለቅ።

ጸናጽሌን ልያዝ ከበሮዬን  ልምታ፣

ዓለም ግሩም ትበል ታምርህን አይታ።

((©ጌች ቀጭኑ)):ገዳም ሰፈር
ሐምሌ 4/2009 ዓ.

No comments:

Post a Comment