Monday, December 28, 2015

አበጀ በለው(1)

ፀሐይ አያጠቁረው ውርጭ አያከስለው፣
ራብ አያከሳው ጥም አያዝለው፣
ድካም አይሰማው እንቅልፍ አይጥለው  ፣
ጎራዴ አያቆስለው ጥይት አይገድለው፣
ስጋ እንዳልለበሰ እንደ ሌላው ሰው፣
ይሄ ሁሉ ጣጣ በሰው ላይ ያለው፣
በሱ አለመኖሩ ምን ይሆን መላው፣
የጀግኖቹ ጀግና አበጀ በለው።
ምነው ባደረገኝ ጋሻ ጃግሬውን፣
ስከተል እንድኖር ኋላ ኋላውን፣
ምነው ባደረገኝ ደበላ ድጉን፣
ወይም ባደረገኝ እጥፍ ዝናሩን፣
ዙሪያ ተጠምጥሜ እንዳቅፍ ወገቡን፣
ምነው ጠመንጃውን ባረገኝ እግዜር
ከደረቱ ሳልወርድ አቅፎኝ እንድኖር።
እዚህ ተቀምጨ ከምኖር በደስታ፣
እረፍት ሳያምረኝ ወገቤን ሳልፈታ፣
አንተን ተከትየ ከጥዋት እስከማታ፣
በጎንቻ በረሀ ልበል ገልታ ገልታ፣
እንቅፋት ሲመታህ አብሬህ ልመታ።
አበጀ በላቸው የመብቴ ጠባቂ ያርነቴ ጌታ።
ምጣዴን አዝዬ እርኮቴን አንግቼ፣
ሽንብራ ቆርጥሜ ጥር ዉሀ ጠጥቼ፣
ራበኝ ደከመኝ ላልል ተገዝቼ፣
ባለ ጸጋ ባሌን ዛሬውን ፈትቼ፣
እሱን እንድከተል ቤት ንብረቴን ትቼ፣
የእግሩ አጣቢ እንድሆን ግርድና ገብቼ፣
አበጀን አማልዱኝ ዘመድ ወዳጆቼ።
የራስ የደጅ አዝማች ምሽት ከመሆኔ፣
አሽከር ከመላኬ ስጋር ከማስጫኔ፣
ስባንን እንድኖር ሳይከደን አይኔ፣
እንቅልፍ እንዳልጠግብ ተኝቼ በጎኔ፣
የእሱ ገረድ ሆኘ ልኖር መለመኔ፣
ወንድ ብወድ ነው ሴት ስለሆንሁ እኔ
ስማኝ ያገሬ ወንድ ልውቀስህ ወቀሳ፣
አይደለህ ቀማኛ አይደለህ ጀውሳ፣
ሳትሰርቅ ሳትቀማ ሳይኖርህ አበሳ፣
እየነዱ ሲያስሩህ  እንዲሁ ባፈሳ፣
የማትንፈራገጥ የምትንቀሳሳ፣
ትንሽ የማትሻክር ከሆንክ ለስላሳ፣
በሁለት እግሩ ቆሞ ከሚሄድ እንስሳ፣
ወይም ነፍስ ከሌለው ከወደቀ ሬሳ፣
ከቶ ልዩነትህ በምንላይ ነውሳ።
በነሴና እነብሴ በነማይ በጎንቻ፣
ወንዱ ሁል ሴት ሆኖ ከቀረ አንድ ብቻ፣
ለቀማኞች መቅጫ ላመጸኞች መምቻ፣
ለደካሞች ምሽግ ጋሻ መመከቻ፣
ለእሱ ተሸክሜ ውሃ በቅምጫና ጥሬ በስልቻ፣
እንኳን በማውቀው ዱር በማውቀው ስርቻ፣
ስሄድ አልኖርም ወይ እስ'ካገር ዳርቻ።
ሌሎች ሲበደሉ እሱ መከፋቱ፣
ሌላ ሰው ሲጠቃ እሱ መቆጣቱ፣
የሰው ቁስል አሞት እንዲህ መሰቅየቱ፣
ግፍን እና አመጽን እንደ መርዝ መጥላቱ፣
ህይዎቱን ለሰው መብት ዋጋ አርጎ መስጠቱ፣
ግርማው እንደ አንበሳ ሲያዩት ማስፈራቱ፣
ምን ከባህር አሸዋ ቢበዛም ጠላቱ፣
ጎራዴውን መዞ አውጥቶ ካፎቱ፣
ብቻውን ብቅ ሲል መድረሻ ማጣቱ፣
ሳያሰናክለው ጋራው ቁልቁለቱ፣
ሃይሉን ሳይቀንሰው እራቡ ጥማቱ፣
እርቀት ሳይገታው እንደ'ሳብ ፍጥነቱ፣
እነሴ ነው ሲባል ጎንቻ መታየቱ፣
ይህን ሁሉ ባህርይ ይዞ መገኘቱ፣
አይመሰክርም ወይ ሰው ከተሰራበት
ከጎስቋላ ጭቃ ላለመሰራቱ።
ጥንቱኑ ሲፈጠር ሲወለድ ከናቱ፣
የሰው ቤዛ እንዲሆን ታዞ ለመምጣቱ፣
አየ ምን ያደርጋል በከንቱ መመኘት
የማይገኝ ነገር፣
ባይሆንማ ኖሮ ሹመት እንደቂጥኝ
የሚወረስ በዘር፣
ቅን ፍርድ ለመስጠት ሰው ለማስተዳደር፣
የያንዳዱን ደሃ መብት ለማስከበር፣
ለዚህ ለተጠቃ ለተበደለ አገር፣
መድሃኒት እንዲሆን እሱን መሾም ነበር።

                        ምንጭ፦ፍቅር እስከ መቃብር

Friday, December 18, 2015

490

      መንገደኛው ዛሬ ሽምግልና ተቀምጬአለሁ።ሁለት ላለመስማማት የተስማሙ ጓደኛሞችን ለማስታረቅ ነበር የተቀመጥነው።አብሮ አደጎች፣አብረው ብዙ ያሳለፉ የጋራ ትዝታዎቻቸው፣የጋራ ደስታቸው፣የጋራ ኀዘናቸው የበረከተ ወዳጆች ነበሩ።ሆኖም አሁን ግን የተስማሙት ላለመስማማት ነው።አንዱ አንዱ የሚናገረው አይጥመውም፣የሚተያዩት በትዕቢት ዓይን ነው።ክፉኛ ተናንቀዋል{በሁለቱም ሊተረጎም ይችላል}በየንግግራቸው ውስጥ እንደ አዝማች የሚጠቀሙት ደግሞ "አላውቅህም ወይ?" የሚል ዜማ አለ።የሚነጋገሩት ላለመረታት ነው።ቆይተው ደግሞ "ጉድህን ነው የማወጣልህ! ጎድህን ነው የማዝረከርክልህ!" ይባባላሉ።ሁለቱም ጓደኛሞች ግን ማተብ ያሰሩ፣ቤተክርስቲያን የሚስሙ ክርስቲያኖች ነበሩ።የጠባቸው መንስኤ ተብል የሚቀርበው ነገር እዚህ ግባ የማይባል ተራ ነገር ነው።እንኳን ብዙ ያሳለፉ አብሮ አደጎች በቅርቡ የተገናኙ ሰዎች እንኳን ሊጣሉ የማይችሉበት ተራ ምክንያት።አንዱ ሲናገር ሌላኛው ስሩ ይገታተራል።"ልብ አድርጉልኝ እያዋረደኝ ነው! ልታሰድቡኝ ነው እንዴ? የጠራችሁኝ!" ይላል።ተናጋሪው ደግሞ ፊቱ በድል አድራጊነት ያበራል።እኔ ግን ከተነገሩት ነገሮች የትኛው ስድብ እንደሆነ የትኛው እንደሚያዋርድ አልገባህ ብሎኝ ተቸገርሁ።"በደንብ አልሰማሁ ይሆን? "ብየም ተጠራጠርሁ።ሆኖም እነርሱ የተግባቡበት ውስጣዊ ቋንቋ ነበር።ነገሩን እንደምንም አብርደን ልናስታርቃቸው ሞከርን።ሆኖም ላይስማሙ የተስማሙት ጓደኛሞች ቃላችንን ሊሰሙ አልፈለጉም። የእርቅ ጉዳይ ሲነሳ ሁለቱም ነብሮች ሆኑ።ማሉ ተገዘቱ።"ወይ ክርስትና "አልኩኝ በልቤ።"ጠላቶቻችሁን ውደዱ" የሚለው ቃል ለካ ጥቅስ ብቻ ነበረ።ቃሉን ለመስማት እንጅ እንደቃሉ ለመኖር የሚፈቅድ ማንም የለም።የማውቀውን መጽሐፍ ቅዱስ ቃል ልናገር ስሞክር አንድ አንዴ ቀድመው ያብራሩልኛል፣አንደ አንዴ ደግሞ "እርሱ መጽሐፍ ቅዱስ ነው። አሁን ከዚህ ጋር ምን አገናኘው?" ይላሉ።አሁን ላይ ያልተጠቀምንባት ወንጌል ለመቼ ልትሆነን ነው?ሁለቱ  ስመ እግዚአብሔርን እየጠሩ ማሉ ተገዘቱ። ዕርቅ የሚሻውን አምላክ ስም ጠርተው አንታረቅም አሉ።ምክንያታቸውን ስንጠይቃቸው "በቃ እንዲሁ ከእርሱ ጋር መቀጠል አልፈልግም" ከማለት ውጪ ሊታረቁ ላለመቻላቸው አንዳች በቂ ምክንያት አላቀረቡም።ይህን ጊዜ "አለሙን እንዲሁ ወድዷል" የሚለው ቃል ትዝ አለኝ።እኛን ለመጥላት ብዙ ምክንያት እያለው እንዲሁ የወደደንን አምላክ "እናምናለን" እያልን እንዲሁ አስጠላኸኝ መባባላችን እንዴት ያሳዝናል።ከሁሉ የገረመኝ አንዳችን ተነስተን ከቃለ እግዚአብሔር እየጠቀስን ለደቂቃወች ስናወራ በጸጥታ ካዳመጡን በኋላ ንግግራችንን ከምንም ሳይቆጥሩ አቁመው እንዳስቀጠሉት ቴፕ ያንኑ ንግግራቸውን መቀጠላቸው ነው።

Tuesday, December 08, 2015

ሰላም

ብላቴናው ወንድማችሁ ሰሞኑን በአንዳንድ የሃገራችን ከተሞችና ዩኒቨርሲቲዎች በተከሰተው አለመረጋጋት ምክንያት ነፍሴ መረበሽ ከጀመረች ቀናትን አስቆጥሪያለሁ።ነግሩን ለመጀመሪያ ጊዜ የሰማሁት በጅማ ዞን በሚገኘው የመረዋ ተክለሃይማኖት ገዳም የሰብል ስብሰባ መርሃ ግብር ስለነበር የበረከቱ ተካፋይ ለመሆን በሄድሁበት ዕለት ነበር።ለ 30 ደቂቃያህል በቆሎ ስንቃርም ከቆየን በኋላ በብፁዕ አባታችን ትዕዛዝ  ስድስት ሰወች ለጤፍ ሸክም  እንድንሄድ ተደረገ።በዚህ ሁኔታ ላይ ሳለን ለአንዱ ጓደኛየ ስልክ ተደውሎለት ለተወሰኑ ደቂቃዎች ሲነጋገሩ ከቆዩ በኋላ በአንድ ግቢ በተከሰተ ሁከት ምክንያት የሰው ህይወት ማለፉንና የእርሱን ደህንነት ለመጠየቅ እንደደወሉለት ነገረኝ።እውነት ለመናገር መጀመሪያ ላይ ለጉዳዩ ትኩረት አልሰጠሁትም ነበር።ኧረ! እንዲያውም ተማሪን ለማስደንበር የተፈጠረ ዉሸት መስሎኝ ነበር።ዉሎ ሲያድር ግን ነገሩ ተጠናክሮ የወሬ ማዕበል ከየአቅጣጫው ይጎርፍ ጀምሯል።አንዱ በእንትና ከተማ ይህን ያህል ሰው ሲሞት፣ በእንትና ዩኒቨርሲቲ ይህን ያህል ሰው ቆሰለ ይላል። ሌላውም ብድግ አድርጎ "የለም እነዚህ የመንግስት መገናኛ ብዙሃን ነገሩን ሸፋፍነውት ነው እንጅ የሟቾች ቁጥር ብቻ እንኳን ወደዚህ ከፍ ሳይል አይቀርም" ይላል።የሆነው ሁኖ ብላቴናውን ፍርሃት ክፉኛ ይንጠኝ ጀምሯል።ምነው ገረማችሁሳ? ወንድ ልጅ አፉን ሞልቶ "ፈራሁ" ሲል ብትስቁም አይደንቀኝም፤ ምክንያቱም እናንተ የፌደራል ፖሊሶቹን ከስክስ ጫማ ምን እንደሚመስል አታውቁማ።ብታውቁ ኑሮ ግን እንደ እኔ የዶርማችሁን በራፍ በቁም ሳጥን  ጥርቅም አድርጋችሁ ዘግታችሁ አልጋችሁን የሙጥኝ ማለታችሁ እንደማይቀር በእርገጠኝነት መናገር እችላለሁ።እኔን ግን ሚገርመኝ ባልፈራ ነበር።በዚች የቀንበር ቅንጭርት የሰበረ ኮርማ  ጭድ ሲሰጠው ቀና በሬ በጅማት ቁግ እየተገረፈ እስከ ማታ በሚያርስባት፣አጉራ ሰብረው የወጡ ጊደሮች በመላሾ ተደልለው ወደ ጋጣቸው ሲመለሱ ገራም ላሞች ቀፈዳቸው እስኪበር በሽመል እየተወቁ በሚታለቡባት፣ፍየሎች ተለቀው በጎች በሚኮደኮዱባት፣በእጅ ሚዳሰሰውን የሲኦልን ጨለማ የለበሰ ሰይጣን በጭብጨባ ሲሸኝ ፀሐይን የተጎናጸፈው የብርሃን መልአክ መከናነቢያውን እንዲያወልቅና እርቃኑን እንዲሄድ  በሚደረግባት፣በርባንን አስፈትታ ክርስቶስን በምታሰቅል፣በዚች እጆቿ በንፁሃን ደም የተጨማለቁባት የአመጸኞች ዓለም እየኖርሁ መፍራት ይነሰኝ?የመፍራት መብት አንቀፅ ስንት ነበር እባካችሁ?ላለፉት ሁለት ሳምንታት እረፍት ላይ ስለነበርሁ ጊዜየን ማሳልፈው አንዳንድ አዝናኝ የሆኑ ነገሮችን በማንበ አልያም በማየት ነበር።ትናንትና ማታም የጓደኛየን ላፕ ቶፕ ተውሸ "ከቃል በላይ"የተሰኘውን አማርኛ የፍቅር ፊልም እያየሁ በነበረበት ሰዓት ከወደ ውጭ የመጣ የጩኸት ድምፅ ጭርር... ሲል ሰማሁ።የግቢ ተማሪወች የፌደራል ፖሊስ ሲያዩ የሚያሰሙት ፍርሃት የቀላቀል የቅዠት ጩኸት ነበር።ፊልሙን እንደምንም ጨርሸ መብራቱድ ድርግም አድርጌ ካጠፋሁ በኋላ ጎኔን ካልጋው ባገናኝም እንቅልፍ ግን ሊይዘኝ አልቻለም።በምትኩ አእምሮዬ የተለያዩ ጥያቄዎችን እያነሳ ሲያወጣና ሲያወርድ ሌሊቱ ተገባደደ።ሁከት ምንድን ነው? የሁከት ፈጣሪዋ ማን ነው? አላማውስ ምንድ ነው? ዉጤቱስ?   ከሁከት በተቃራኒ ያለው፤ ሰላምስ ምንድ ነው? መገኛውስ ከወዴት ነው? ይህች ዓለም ሰላሟን እንድታጣ የሚደርጓት ነገሮችስ ምንድን ናቸው?እና የመሳሰሉት።

Thursday, December 03, 2015

የግቢ ማስታወሻ

ሰላምይሁን ተውልዶ ያደገው በባህር ዳር ከተማ  ሲሆን የህይወት አስቸጋሪ ውጣ ውረዶችን የጀመረው ገና በሕጻንነት እድሜው እንደሆነ የሚያውቁት ይናገራሉ። ከዕለታት አንድ ቀን መሐል ፒያሳ ላይ ቆሟል። ምን ማድረግ እንዳለበትም ሆነ የት መሄድ እንዳለበት በትክክል ። መለየት ተስኖታል። በዚያ ላይ ረሀብ በጣም እያስቸገረው ነው። ሲያስበው ትናንትና ጥዋት ላይ ምግብ ወድ አፉ መጠጋቱ  ትዝ አለው። ያለው ብቸኛ አማራጭ ሁሌም ሰዎች ሲያደርጉት የሚያናድደውን ተግባር እርሱም መፈጸም እንደሆነ አመነበት። እናም ከአራዳ ጊዮርጊስ ወደ መብራት ኃይል ሕንፃ በሚወስደው የግራ መስመር ላይ ቆሞ ታክሲ ለመሳፈር ከሚጋፉት ሰዎች አጠገብ ደረሰ። ልቡ በአፉ በኩል ወጥታ ለመሄድ የምትታገለው እስኪመስለው ድረስ ፍርሃት እየናጠው ታክሲ ጥበቃ አጠገቡ የቆመውን ሰው ማናገር ጀመረ። ግን ገና ፊቱ ለመለመን መዘጋጀቱን በሚያሳይ ሁኔታ ሲቅለሰለስበት "እግዚአብሔር ይስጥህ" ብሎት ቦታ ቀየረ። አሁን ሰላምይሁን አይኖቹ እንባ አቀረሩበት በዚህ መንገድ መለመን ከቀጠለ ማንም ምላሽ እንደማይሰጠው ወዲያውኑ ተገነዘበ። እንደ ምንም ብሎ ወደ ኋላ በማፈግፈግ አንድ ጥግ ላይ ተቀምጦ ቀጥሎ ማድረግ ያለበትን ነገር ማውጠንጠን ተያያዘ።


ጭንቅላቱ መፍትሄን ከመፈለግ ይልቅ "ለምን ይህ ሁሉ በእኔ ላይ ሆነ?" የሚለው ጥያቄ ፋታ ሊሰጠው አልቻለም። ወደ ላይ እና ወደታች የሚራወጡትን የአዲስ አበባ መኪናወች፣የሰዎችን ሩጫና የተደበላለቀውን ጩኸት ሲያስተውል በእርሱ ውስጥ ያሉ የሃሳብ ብዛት በአካል የታዩ መስሎት ፈገግ ማለት አሰኘው። በፊት ሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን በመከራ ጨርሶ ዩኒቨርሲቲ ከገባ በኋላ ሁሉም ነገር ይስተካከላል በማለት ሲመካ የነበረው ነገር ጭራሽ ሁሉም ነገር ተዘበራርቆ ለእርሱ ዩኒቨርሲቲ የምድር ሁሉ መከራ መለማመጃ መሆኑ ሁሌም ይገርመዋል። የሚወዳቸው እናቱ በአስጊ ሁኔታ የኩላሊት በሽተኛ ስለሆኑ ምን ማድረግ እንዳለበት ተስኖታል። እርሱ የጀመረውን የኢንጂነሪንግ ትምህርት ጨርሶ ለመውጣና እናቱን ለመጦር ከሚያልመው የበለጠ ሌላ ተስፋ በህይዎቱ ውስጥ አለኝ ብሎ አስቦ አያውቅም ነበር። አባቱ በድንገተኛ የመኪና አደጋ ምክንያት ለስራ በወጡበት ሳይመለሱ በመቅረታቸው ገና ክርስትና ከተነሳበት ሳምንት ጀምሮ እናቱ በመከራ ነው ያሳደጉት። እናቱ ወ/ሮ ብርሃን ለእርሱ በትክክል የሕይወቱ ብርሃን መሆናቸውን ያምናል፤እርሳቸው ከሌሉ አበቃ! ብርሃኑም ይጠፋል። ይህ ነው የሰላምይሁን ጭንቀት።

Friday, November 27, 2015

ጥጡና ፈታይዋ

ባበባነት ወቅቱ
ጥጥ ነኝ ብሎ ቀርቧት
ፈታይ ሆና ቀርባው
ከስሩ ፈንቅላው
ከንቡጡ ፈልፍላው
ከ'ማረጉ አውርዳ
መሬት አስተኝታው
በፈገግታ በትር በሳቅ ማዳወሪያ
ቀኑን ሙሉ ወቅታው
በድምጧ መንደፊያ
ባ'ይኗ መዳመጫ
ከፍሬው ለይታው
ለካ እሱም ተረቶ
ሰውነቱን ትቶ
{አምኖ ጥጥነቱን}
መዳፏ ስር ገብቶ
ድድር ገላው ላልቶ
ኾኖላት ባዘቶ
በስሜት እንዝርቷ
ታብቶላት አስራው
በራቁት ጭኗ ላይ
አሽከርክራ አሹራው
ሲወፍር አቅጥናው
ሲረግብ አክርራው
ሲያሰኛት ልቃቂ
ሲያሻት ቀለም አርጋው
ለካ እሱም ተረቶ
ሰውነቱ ትቶ
ጥጥነቱን አምኖ
እንዳደረገችው እንዳሰኛት ሆኖ
መለወጡን እንኳ ሳያስብ ላንድ አፍታ
ከጥጥነት ልቆ ሆኗት ቀጭን ኩታ
ቀነቀን ለውበቷ
ማታ ለሙቀቷ
ሲሆን ሰነባብቶ
ዕድፍ እና ትቢያ ከገላዋ አንስቶ
ጸዐዳው አከሉ እያደር ጨቅይቶ
እሷ ሳትለውጥ
እሱ ነትቦ አርጅቶ
ተሽቀንጥሮ ቀረ ሆነና ቡትቶ
በሌላ ጸዐዳ ኩታ ተተክቶ
                   ስብስብ ግጥሞች
                            በውቀቱ ስዩም

Wednesday, November 25, 2015

ጽፈሽ ያዥው ይጠቅምሻል!

ላንቺ ይባልኝ እንጅ ቃልሽ ለፈረሰው፣
እኔስ እኖራለሁ እንደ ሰው እንደ ሰው። አዎ! ላንቺ ነው፤ ከገባሽ ይግባሽ አዎ! ላንቺ ነው፤ ሳምንሽ ለከዳሽኝ ድንገት የተግባባን መስሎኝ ልቤን ሰጥቸሽ ዘነጣጥለሽ ላስረከብሽኝ።ይሄው! ይሄው! እድሜ ላንቺ የተሰበረ ልቤን ጥገና ያልሄድሁበት ያልዞርሁበት ቦታ የለም።ግን መድሃኒቱ ካንቺ ዘንዳ ሆኖ ከየት አባቴ እንደማገኘው ግራው ገብቶኝ ስጨነቅ እኖር ነበር። አሁን ግን እግዚአብሔር ይመስገን ልቤ ወደ ነበረበት ተመልሷል።እንዳንቺማ ቢሆን ኖሮ ልቤን አጥቸ እየተሰቃየሁ እኖር ነበር። ግን ፈጣሪ አለሁልህ አለኝ።ታስታውሻለሽ ያኔ በፊት በፊት የሰማዩን ከዋከብት የምሽቱን ጨረቃ የቤታችን አምፖል አንቺ ሆነሽ የምበላበት ሳህን የምማርበት ደብተር ዉስጥ እየተገኘሽ ሰላሜን አሳጥተሽኝ በህልሜም እየመጣሽ እንቅልፍ ነስተሽኝ ነበር።ጨረቃም ከዋከብትም አምፖልም ሳህንም አንቺው ሆነሽብኝ ይህችን አለም ላንቺ አድርጌ ስያት ነበር።ለካ አንቺ ለዚችች አለም ኢምንት! ኢምንት! ኢምንት! ነሽ።አሁን ላይ ግን ልንገርሽ ውዴ!ጨረቃውም ጨረቃ ከዋከብቱ ከዋከብት አምፖሉም ሳህኑም ያው ራሳቸው ናቸው። ለካ ያኔ አእምሮየ ውስጥ አግዝፌ ስየሽ ስለንነበር ነው እንደዚያ ራሴን ጥየ ስሰቃይ የኖርሁት።ግን እንዴት አስቻለሽ ያን ሁሉ ስቃየን ያን ሁሉ ጭንቀቴን ያን ሁሉ ችግሬን  እየነግርሁሽ፤ ትንሽ ሰወኛ ስሜት ያልተሰማሽ ለምን ነበር? ምላሹን አልፈልገውም። ጽፈሽ ያዥው ይጠቅምሻል።የሆነው ሆኖ ለህይወቴ ትልቁን ትምህርት ሰጥተሽኛል።ተሰብራ የነበርችውን ልቤን ድጋሜ እንዳትሰበርብኝ አርቄ እንዳስቀምጣት ስለረዳሽኝ አመሰግናለሁ።በተረፈ የእጅሽን ይስጥሽ አልልሽም።ምክንያቱም የዛሬን አያርገውና በአንድ ወቅት ለህይወቴ መሰርታዊ ከሆኑት ነገሮች ማለትም ምግብ፣ መጠጥ፣ መጠልያ እና ልብስ ጋር ተደምረሽ የነበርሽ፤ ነገር ግን በራስሽ ምክንያት ራስሽን የቀነስሽ ሴት ነሽ።ስለዚህ ከልቤ ከልቤ የምመኝልሽ መልካሙን ሁሉ እንዲገጥምሽ ነው።በተረፈ ይሄን ዘፈን ላንቺ ሳይሆን ለምስኪን አፍቃሪዎች ጋበዝሁኝ።
      አፍቅሬ እያመንኩኝ ሳልጠላሽ፣
      አስችሎሽ እምነቴን ከበላሽ።
     ላንቺ መባል ይብቃኝ ከእንግዲማ፣
    ሃገር ይወቅልኝ ሁሉም ይስማ።
    ለፍቅርሽ ስጨነቅ ስጠበብ ከርሜ፣
    ለክብርሽ ስሟገት ስምሽን አንግቤ፣
    በዚያ በክፉ ቀን ሳጣሽ ካጠገቤ፣
   ፍም ይወጣኝ ነበር እንደመንገብገቤ።
                  ያንችው  አፍቃሪ

Friday, November 13, 2015

ፋኖስና ብርጭቆ

አንድ የፋኖስ መብራት በግብሩ የኮራ፤
እንዲህ ሲል ተጣላ ከብርጭቆ ጋራ፡፡
‹‹እኔ ነኝ መብራቱ ብርሃን የምሰጥ፤
ጨለማን አጥፍቼ የምገላልጥ፡፡
አንተ ግን ከፊቴ እንዲህ ተደንቅረህ፤
ዙሪያዬን ከበኸኝ እንዲያው ተገትረህ፡፡
አልገባኝም ከቶ የምትሰራው ስራ፤
ብርሃኔ ሩቅ ደርሶ ደምቆ እንዳያበራ፤
አንተን ፈጠረብኝ መንገድ የምትዘጋ፡፡
እንቅፋት እየሆንክ ስራዬን አታጥፋ ፤
ገለል በል ከፊቴ ብርሃኔ ይስፋፋ፡፡››
(ብርጭቆም ሲመልስ)
‹‹አገልግሎቴማ ከሆነብኝ ጥፋት፤
እውነት እኔ ላንተ ከሆንኩህ እንቅፋት፡፡
ልሂድልህ›› ብሎ ሲለቅለት ቦታ፤
ከጎን የነፈሰ የንፋስ ሽውታ፣
መጣና መብራቱን አጠፋው ባንዳፍታ፡፡
አጭር እየሆነ ተመልካችነቱ፣
መለየት አቅቶት ጥቅሙን ከጉዳቱ፣
እወቁኝ እወቁኝ እያለ ሲነሳ
ሰውም እንደዚሁ ያመጣል አበሳ፡፡

Friday, October 30, 2015

መለየት

የለም! የለም!
መለየት መሞት አይደለም፣
ሞትም መለየትን አያክለው ፣
መለየትም ሞትን አይመስለው፣
ትርጓሜአያቸው ለየቅል ነው፣
አንቺም እኔም ጅረት ሆነን፣
ከራሳችን ምንጭ ፈልቀን፣
በራሳችን ፈለግ ፈሰን፣
ህይወት በሚሉት መቅበዝበዝ
አገር ምድሩን አዳርሰን፣
ሄደን!ሄደን! ሄደን! ሄደን!
ወርደን!ወርደን!ወርደን!ወርደን!
ሞት በሚሉት ውቅያኖስ
አንድ ስንሆን ተዋህደን
ተገናኘን እንበል እንጅ
መች ጨርሰን ተለያየን
      የለም!የለም!
መራቅ መለየት አይደለም፣
ሰው በሰወች ግዞት፣
ችግር ይዞት፣
አገር ቀየውን ጥሎ፣
ስልቻውን በጫንቃው አዝሎ፣
ቅሉን ጨርቁን አንጠልጥሎ፣
ብቻውን ሄደ ቢለው ሰፈርተኛው ተጃጅሎ፣
እርሱ በልቡ ህንጻ በማይዘመው በማይፈርሰው፣
 ከተጓዘ አኑሮ ሰው፣
እውን ይሄ መለየት ነው
የለም! የለም!
መለየት ይህ አይደለም
ትርሚያቸውን እንቀይረው፣
ላንቺ እና ለኔ ሌላ ነው፣
ከፊቴ ቁጭ ብለሽ
ከፊትሽ ቁጭ ብየ፣
ክንድሽን ካንገቴ ጥለሽ
ክንዴን ካንገትሽ ጥየ፣
የምታወሪው ሳይገባኝ
ራሴን ስነቀንቅ፣
የማወራሽ ሳይገባሽ
ለይስሙላ ጥርስሽ ሲስቅ፣
ቻው ቻው ሲለኝ ቀልብሽ፣
ደህና ሁኚ ሲልሽ አይኔ፣
መለየት ይህ ነው ለኔ።

Thursday, October 15, 2015

ልባም ሴት

      ልባም ሴትን ማን ሊያገኛት ይችላል? ዋጋዋ ከቀይ ዕንቍ እጅግ ይበልጣል።የባልዋ ልብ ይታመንባታል። ምርኮም አይጐድልበትም።ዕድሜዋን ሙሉ መልካም ታደርግለታለች፥ ክፉም አታደርግም።የበግ ጠጕርና የተልባ እግር ትፈልጋለች፥ በእጆችዋም ደስ ብሎአት ትሠራለች።እርስዋ እንደ ነጋዴ መርከብ ናት፤ ከሩቅ አገር ምግብዋን ትሰበስባለች።ገና ሌሊት ሳለ ትነሣለች ለቤትዋም ሰዎች ምግባቸውን፥ ለገረዶችዋም ተግባራቸውን ትሰጣለች።እርሻንም ተመልክታ ትገዛለች፤ ከእጅዋም ፍሬ ወይን ትተክላለች።ወገብዋን በኃይል ትታጠቃለች፥ ክንድዋንም ታበረታለች።ንግድዋ መልካም እንደ ሆነ ትመለከታለች፤ መብራትዋ በሌሊት አይጠፋም።እጅዋን ወደ አመልማሎ ትዘረጋለች፥ ጣቶችዋም እንዝርትን ይይዛሉ።እጅዋን ወደ ድሀ ትዘረጋለች፥ ወደ ችግረኛም እጅዋን ትሰድዳለች። ለቤትዋ ሰዎች ከበረዶ ብርድ የተነሣ አትፈራም፥ የቤትዋ ሰዎች ሁሉ እጥፍ ድርብ የለበሱ ናቸውና።ለራስዋም ግብረ መርፌ ስጋጃ ትሠራለች ጥሩ በፍታና ቀይ ግምጃ ትለብሳለች።ባልዋ በአገር ሽማግሌዎች መካከል በሸንጎ በተቀመጠ ጊዜ በበር የታወቀ ይሆናል። የበፍታ ቀሚስ እየሠራች ትሸጣለች፥ ለነጋዴም ድግ ትሸጣለች። ብርታትና ከበሬታ ልብስዋ ነው፤ በኋላም ዘመን ላይ ትስቃለች። አፍዋን በጥበብ ትከፍታለች፤ የርኅራኄም ሕግ በምላስዋ አለ። የቤትዋንም ሰዎች አካሄድ በደኅና ትመለከታለች፥ የሀኬትንም እንጀራ አትበላም። ልጆችዋ ይነሣሉ፥ ምስጋናዋንም ይናገራሉ፤ ባልዋ ደግሞ እንዲህ ብሎ ያመሰግናታል። መልካም ያደረጉ ብዙ ሴቶች አሉ፥ አንቺ ግን ከሁሉ ትበልጫለሽ። ውበት ሐሰት ነው፥ ደም ግባትም ከንቱ ነው፤ እግዚአብሔርን የምትፈራ ሴት ግን እርስዋ ትመሰገናለች።መ/ምሳሌ 31:10-31

Saturday, July 11, 2015

የፍጻሜ ልዑል

የፍጻሜ ልዑል
በገፍ እየጠጣ ወንዝ እና ዝናሙን ባህሩ ካልረካ፣
በጅምላ እያቀፈ ፀሐይ ከዋከብቱን ጠፈሩ ካልፈካ።
በቀረብነው ቁጥር ግባችን ከራቀ፣
የተጀመረ እንጅ ባይኖረን ያለቀ፣
ጣእመ ህላዌ እንዳይሆን መራራ፣
ቅስም እንዲያንሰራራ፣
መሃላችን ካለ
ባ'ለ ብዙ ጅምር ባለ ሺህ ሙከራ፣
የፍጻሜ ልዑል ተብሎ ይጠራ።
ምንቸት እና ጋን
ይኑር እንጅ ባ'ገር፣
በቀየ በሰፈር፣
ኩሬ ሙሉ ዉሃ ምድጃ ሙሉ እሳት
ዳውላ ሙሉ አፈር፤
የምንቸቶች ስፍር መች በጋን ይለካል፣
ጋኖች እንኳን ቢያልቁ ሌላ አፈር ይቦካል።

ምንጭ፦ ስብስብ ግጥሞች
                               በውቀቱ ስዩም

Friday, June 05, 2015

የነፍስ እና የስጋ ቡጢ

ጊዚያችን ካለፈ እንዳይቆጨን ኋላ፣
እንዝፈን አንዝፈን እንጹም እንብላ፣
እንስጥ እንቀማ እየተባባሉ፣
ነፍስ እና ስጋየ በፈቃድ ተጣሉ።
የሚያስታርቃቸው ሽማግሌ ጠፍቶ ፣
ደግሞ ላይስማሙ ጠባቸው ጎርንቶ።
በስድሳ ዙር ቡጢ ደግሞ በሰማኒያ፣
እጅግም ቢበዛ መቶ መቶ ሃያ፣
ቆርጠው ሊፋለሙ ተፈላለጉና፣
ወደ ሜዳ ገብተው ባንድ ላይ ቆሙና፣
ለየደጋፊያቸው ንግግር ሲኣደርጉ፣
ስጋ ብቻ ነበር የሚታይ በወጉ።
ከመድረኩ ቆሞ ስፎክር ሲያገሳ፣
ማን እንደሱ ጀግና ማን እንደሱ አንበሳ።
ነፍስ ግን በፍርሃት እንደሌለች ሆና፣
ደጋፊወቿንም እጅግ አሳዝና፣
ትታይ ነበረ ገርጥታ ኮስምና።
ዳኛው ፊሽካ ነፍተው ሲጀመር ያ ጣጣ፣
ስጋ ተንደርድሮ ሊያቀምሳት ሲመጣ፣
ነፍስ አሳለፈችው አቅጣጫ ለውጣ፣
ቁጭ ብድግ ብላ ሩጣ ተራውጣ።
ልትዘል ስትሞክር በስተኋላ ዙሮ፣
ሰንጎ ያዘና የነፍስን ጉሮሮ፣
ሲያጣድፋት ጊዜ በእርግጫ በጡጫ፣
በስተሃያኛው ዙር አጣች በግቢያ መውጫ።
የነፍስ ደጋፊዎች ሲያዝኑ ሲሳቀቁ፣
ዳኛው ስጋን ገፍተው ነፍስን አስለቀቁ።
ጉሮሮ በማነቅ ፋውል በመስራቱ፣
ስጋን ተቆጥተው መከሩ ዘበቱ።
መላ ቅጥ ቢያሳጣት የሥጋ ጨዋታ፣
እንደማያዋጣት መዝና ገምታ፣
በግርግር መሃል ባገኘችው ፋታ፣
ነፍስ ሾልካ ጠፋች ፉክክሩን ትታ።
አሸናፊነቱ ጀግንነቱ ታውቆ፣
አስጨንቆ ይዞ ሳያስቀራት አንቆ፣
ታታው እነድሄደች ስጋ ይህን አውቆ፣
ያለቅስ ጀመረ ተዝለፍልፎ ወድቆ፣
አይን ጥርሱ ገጦ አረፋን አድፍቆ።
በሀዘን በለቅሶ እራሱ ፈረሰ፣
አመድ ነሰነሰ በአፈር ተለወሰ።
እንዲያ ሲደነፋ ሲዘል የነበረ፣
ከመድረኩ መሃል ስጋ ወድቆ ቀረ።
              ምንጭ፦ ከሰይጣን ጋር የተደረገ ቃለ ምልልስ እና ሌሎች

Tuesday, June 02, 2015

ሰሳ


Yaya-Sanogo
በአንድ የክረምት ወራት ዝናብ እንዳባራ፣
ወጣ አልኩኝ ከቤቴ ቀለል ላለ ስራ።
በጠራው ሜዳ ላይ አንድ የሜዳ ሰሳ፣
አየሁ ሰርዶ ልትግጥ ስትወድቅ ስትነሳ።
አወ ራራሁላት ችግሯን አይቼ፣
ፈለግሁ ልመግባት ከስርዶው ነጭቼ።
ከአጠገቧ ሰርዶ ነቃቅየ ይዤ፣
እሥሥ ብይ ብየ ጋበዝኋትኝ በእጄ።
ጥላኝ ስላልሮጠች አልቆረጥሁም ተስፋ፣
እሷም ቀጥ እኔም ቆምሁ ፍጥጫው ተስፋፋ፣
ከመካከላችን እግር ነቃይ ጠፋ።
ካሰብሁኝ በኋላ አውጥቸ እና አውርጄ፣
ወሰንሁኝ ልሰጣት እኔው ግፋኝ ሂጄ።
አንድ እግሬን አንስቼ ወደ ፊቴ ስጥል፣
እሷም የኋላ እግሯን የኋሊት ስትነቅል።
የግራውን እግሬን ሳነሳው ለአንድ አፍታ፣
እሷም ሸርተት ስትል የኔን እግር አጥታ።
ስትሄድ ወደ ኋላ እኔም ስከተላት፣
በጨበጥሁት ሰርዶ ስጥር ላባብላት፣
ወደፊት አምጥቸ ከሳሩ ላበላት።
እሥሥ አንች ሰሳ ሰላም ነኝ አትፍሪ፣
አገሩም ሰላም ነው ሰውንም ድፈሪ፣
አንችም እንደ ሰወች በነጻነት ኑሪ።
ብየ ብቀባጥር አላዳመጠችም፣
አወ አትናገርም አልተናገረችም፣
ከኋላ ጉዞዋም ፈጽማ አልቆመችም።
እኔም ተስፋ ሳልቆርጥ እርሷም ስትጎትተኝ፣
ሚዳቆች ቡኸሮች ጮቤ እረገጡ፣
ከኋላዋ ካለው ከዱሩ እየወጡ፣
ለጎሪጥ እያዩዋት አልፈዋት እሮጡ።
አፌ ስራ አልፈታምጮሆ ይናገራል፣
ወደፊ ተራመጅ እንደነሱ ይላል።
እየጎተተችኝ በሃሳብ ተውጣ፣
ከስርዶው ልትጎርስ ወደፊት ስትመጣ።
ድንገት ሳታስበው ከጥንት ዘመን ጉድባ፣
ሁለት የኋላ እግሯ ሰርጎድ ብሎ ገባ።
በሁለቱ እግሮቿም ጋማቱን ጨብጣ፣
ሰማሁኝ ለእርዳታ ቃል ከአፏ ሲወጣ።
ጎትቸ ለማውጣት በተቻለኝ አቅሜ፣
ሁለት የፊት እግሯን ያዝሁ ተሽቀዳድሜ።
እየጎተትሁ ሽቅብ አንገቷ ሲወጣ፣
የዝንጀሮ መንጋ ከዋሻው ስር መጣ።
አንዱ አንዱን ረግጦ አንዱ በአንዱ ወጦ፣
አንደኛ ጅራቷን አንዱ እግሯን ጨብጦ።
ያን የገደል ዋሻ ተቆላልፈው ወጥተው፣
ፈለጉ ሊወስዷት ከመዳፌ አውጥተው።
ምን ሊያደርጋት ይሆን የዝንጀሮ መንጋ፣
ከመቸስ ወዲህ ነው የለመደው ስጋ።
ብየ እየጎተትኋት ወደታች ባፈጥ፣
የተራበ አንበሳ አየሁኝ ከዉስጥ።
እኔም ላላስበላት ስጎትት ስትወጣ፣
ጨለማው ተገፎ ታየኝ ቀን ሲመጣ፣
እኔ ብቻ ነቃሁ ሕልሜ ትርጉም አጣ።

የሌሊት ዜማዎች

ተዋናይ ነው አሉ፣
ሞትን የገዘተ ሰባት አመት ሙሉ።
ታዲያ ምን ይደንቃል፣
እንቅልፍን ገዘትሁት እኔ በምስኪን ቃል።
የእድሜወቼን እሸት ቢበላ ቢበላ፣
አሲዳም እንቅልፌ መቼም ከርሱ አይሞላ፣
መደቤን አፍርሼ ከህልሜ ልጣላ።
ተዋናይ ስለምን አምላክን ይከሳል፣
ሞት አንዴ ይመጣል ህልም ይመላለሳል።
መቃብርን ደፍኖ ሞትን በቁም አስሮ፣
ሰው ነፍሱን ይቀብራል ሕልሞቹን ቆፍሮ።
ተዋናይ ምርኮህን ልቀቀው ይፈታ፣
ና! እንቅልፍን እሰር በሞት እግሮች ፈንታ።
በአልጋ እቅፍ ለኖረ ጉድጓድ መች ይከብዳል፣
ከመቃብር ይልቅ ሕልም ይጎደጉዳል።

ገንዘብ

10624745_1730988887125730_7825557555215847685_n
ፍሬ መሬት ወድቆ ከዋለ ካደረ፣
ገንዘብ ሰውን ገዝቶ መቅበር ከጀመረ፤
የመጣ ነውና ቀድሞውን ከጥንት፣
ሁለቱም አይድኑም ከመበላሸት፤
ገንዘብ መፈጠሩ ለሰው አገልጋይ፤
ሆኖ ሊሰራበት አልነበረም ወይ?
አሁን ግን መስገብገብ በጣም ስለበዛ፣
ሰው ባሪያ እየሆነ ለገንዘብ ተገዛ።
ለስሙ ስም አለን ከጥንት እስከ አሁን፣
በእምነታችን ኗሪ ሟች ለክብራችን፣
በማጣት ተወልደን በንጣት አድገን፣
ለገንዘብ እጅ ሰጠ ኩሩልባችን።

መሽቷል አትበል

በውድቅቱ አትከፋ
በጎህ መቅደድ አትጽናና፣
ብርሃን ለመመፅወት አትበል ቀና፣
የእኛ ፀሐይ ሐሩር እንጅ ብርሃን አትወልድምና።
መሽቷል አትበል ጀንበር ስትጠልቅ
ከዛጎሏ ውስጥ ገብታ፣
መሽቷል አትበል ፀሐይ ስትሞት
በከዋከብት ተተክታ፣
በውስጥህ ላለው ብርሃን
ግርዶሽ የሆንህ ለታ፣
ያን ጊዜ ሆኗል ጽልመት
ያን ጊዜ ሆኗል ማታ።
          ስብስብ ግጥሞች ፦በውቀቱ ስዩም