Friday, February 26, 2016

ስማችሁ የለም

በሰማያዊው ዙፋን ዘንድ አንድ ውሳኔ ተላለፈ፡፡ «እነዚህ የኢትዮጵያ ሰዎች ሃይማኖተኞች ናቸው፡፡ ስለዚህም ዓለም ከማለፉ በፊት አስቀድመው ተጠርተው ዋጋቸውን ሊቀበሉ ይገባል» የሚል፡፡ አንድ ሊቀ መልአክ እልፍ አእላፍ መላእክትን አስከትሎ ከሰማይ ሲወርድ ታየ፡፡ በኢትዮጵያ የሚኖሩ ሰዎችንም ሁሉ ለሰማያዊ ፍርድ ሰበሰባቸው፡፡ ወዲያውኑ በመንግሥተ ሰማያት በር ላይ ሁለት ዓይነት ሰልፎች ታዩ፡፡ አንደኛው ሰልፍ ረዥም፤ ሌላኛው ሰልፍ ግን አጭር ነበር፡፡ ረዥሙ ሰልፍ ባለበት ቦታ ገበሬዎች፣ ወዛደሮች፣ የዕለት ሥራ ሠራተኞች፣ እናቶች፣ አባቶች፣ ሕፃናት፣ ሊስትሮዎች፣ የቤት ሠራተኞች፣ ሾፌሮች፣ መሐንዲሶች፣ ሐኪሞች፣ አስተማሪዎች፤ ማን ያልተሰለፈ አለ፡፡ ከጥቂቶቹ በቀር ብዙዎቹ መንግሥተ ሰማያት የመግቢያ ካርድ ማግኘት ቻሉ፡፡ይህንን ሁኔታ ሲመለከቱ በአጭሩ ሰልፍ በኩል የተሰለፉት የልብ ልብ ተሰማቸው፡፡ መጀመርያውኑ ለብቻቸው ሰልፍ የሠሩት ከሕዝብ ጋር ላለመደባለቅ እና ላለመምታታት ብለው ነበር፡፡ እንዴት ሲያስተምሩት፣ ሲያስመልኩት፣ሲያስሰግዱት፣ ሲያሳልሙት፣ ከኖሩት ሕዝብ ጋር አብረው ይሰለፋሉ? መጀመርያ ነገር እነርሱ ያስተማሩት ሕዝብ መንግሥተ ሰማያት ከገባ እነርሱ የማይገቡበት ምንም ምክንያት የለም፡፡ ሁለተኛ ደግሞ ወደፊትም ቢሆን በመንግሥተ ሰማያት ለየት ያለ የክብር ቦታ ሊጠብቃቸው ስለሚችል ለየት ብለው መሰለፋቸው ተገቢ ነው፡፡


ይህንን እያሰቡ እና እያወሩ እያለ አንድ መልአክ ወደ እነርሱ ሰልፍ መጣ፡፡ተሰላፊዎቹ በኩራት ገልመጥ ገልመጥ አሉ፡፡ እንዲያውም «ከመካከላችን ማን ይሆን ቀድሞ የሚገባው» የሚለው ነገር ሊያጨቃጭቃቸው ነበር፡፡ አንዳንዶች በተከታዮቻቸው ብዛት፣ አንዳንዶች በነበራቸው መንፈሳዊ ሥልጣን፣ አንዳንዶች ባገኙት የካሴት እና የመጽሐፍ ገቢ፣ ሌሎችም በሕዝቡ ዘንድ በነበራቸው ተደናቂነት፣ የቀሩትም ደግሞ በንግግር እና በድምጽ ችሎታቸው እየተማመኑ እኔ እበልጣለሁ እኔ እቀድማለሁ ሲባባሉ መልአኩ «እናንተ እነማን ናችሁ?» የሚል ያልተጠበቀ ጥያቄ ጠየቃቸው፡፡ ሁሉም መልአክነቱን ተጠራጠሩት፡፡ አገር ያከበራቸውን፣ሕዝብ ያረገደላቸውን፣እነርሱን ለማየት እና ለመንካት አዳሜ የተንጋጋላቸውን፣ በየፖስተሩ፣ በየካሴቱ፣ በየመጽሐፉ፣ በየመጽሔቱ «ታዋቂው» እየተባሉ ሲቀርቡ የኖሩትን፤ ሰይጣን ያወጣሉ፣ መንፈስ ይሞላሉ፣ ጠበል ያፈልቃሉ፣ እየተባሉ ሲያርዱ ሲያንቀጠቅጡ የኖሩትን፤ ሲዘምሩና ሲያስተምሩ ወፍ ያወርዳሉ የተባሉትን፤ ገንዘብ ከፍሎ መንፈሳዊ ቦታ ተሳልሞ ለመምጣት ሕዝብ ቢሮአቸውን ደጅ ሲጠናቸው የኖሩትን እነዚህን ጉምቱ ጉምቱ ሰዎች የማያውቅ መልአክ እንዴት ሊኖር ቻለ? ተጠራጠሩ፡፡«ለምንድን ነው ለብቻ ሰልፍ የሠራችሁት? ለምን ከሕዝቡ ጋር አልተሰለፋችሁም?» መልአኩ ይበልጥ የሚገርም ጥያቄ አመጣ፡፡ ተሰላፊዎቹ እርስ በርሳቸው ተያዩ፡፡ ከመካከል አንድ በነገሩ የተበሳጨ ሰባኪ «እንዴት እንደዚህ ያለ ጥያቄ በዚህ በመንግሥተ ሰማያት በር ላይ እንጠየቃለን? እስካሁንም ተሰልፈን መቆየት አልነበረብንም፡፡ እኛን ለመሆኑ የማያውቅ አለ? ስንት ሕዝብ ያስከተልን ሰባክያን፤ ስንት ሕዝብ የፈወስን አጥማቂዎች፣ ስንት ሕዝብ ያስመለክን አስመላኪዎች፣ ስንቱን ያስረገድን ዘማሪዎች፤ ስንቱን የታደግን ፈዋሾች፣ ስንቱን የመራን የእምነት መሪዎች፤ ስንቱን በባዶ እግሩ ያስኬድን ባሕታውያን፤ ስንቱን ለገዳም ያበቃን መነኮሳት፤ ሕዝብ ተሰብስቦ የሾመን «ሐዋርያት»፤ እንዴት እነማን ናችሁ ተብለን እንጠየቃለን?» ሁሉም በጭብጨባ ደገፉት፡፡


መልአኩ «መልካም፤ የስም ዝርዝሩን ላምጣውና ስማችሁ እዚያ ውስጥ ካለ ትገባላችሁ» ብሎ አንድ ትልቅ ሰማያዊ መዝገብ ይዞ መጣ፡፡ «እኛ ካልተጻፍን እና የኛ ስም ከሌለ ታድያ የማን ስም በዚህ መዝገብ ውስጥ ሊኖር ነው፡፡ ይኼው እኛ የማናውቀው ሰው ሁሉ እየገባ አይደለም እንዴ?» አለ አንድ አስመላኪ በንዴት፡፡ «ልክ ነህ፤ እናንተ የማታውቁት፣ ፈጣሪ ግን የሚያውቀው፤ እናንተንም የማያውቅ ፈጣሪውን ግን የሚያውቅ ብዙ ሕዝብ አለ ወዳጄ» አለው መልአኩ መዝገቡን እየገለጠ፡፡ «የሁላችሁንም ስም ማስታወስ ስለምችል ሁላችሁም ስማችሁን ንገሩኝ» አላቸው፡፡ ከወዲህ ወዲያ እየተንጫጩ ስማቸውን ከነማዕረጋቸው ነገሩት፡፡ መልአኩ ከፊቱ ላይ የኀዘንም የመገረምም ገጽታ ይነበብበታል፡፡ ቀስ እያለ የስም ዝርዝሩን ያይና ገጹን ይገልጣል፤ ያይና ገጹን ይገልጣል፤ያያል፣ ገጹን ደግሞ ይገልጣል፡፡ ብዙ ሺ ገጾችን ገለጠ፣ ገለጠ፣ገለጠ፤ ማንንም ግን አልጠራም፡፡ ከዚያ ይባስ ብሎ የመጨረሻውን የመዝገቡን ሽፋን ከቀኝ ወደ ግራ መልሶ ከደነው፡፡«ምንም ማድረግ አይቻልም፤ የማናችሁም ስም መዝገቡ ላይ የለም» ብሎ መልአኩ በኀዘን ሲናገር «ምን?»የሚል የድንጋጤ ኅብረ ድምጽ ተሰማ፡፡ «የማናችሁም ስም ወደ መንግሥተ ሰማያት ከሚገቡት ሰዎች ዝርዝር ውስጥ የለም» አለ መልአኩ በድጋሜ፡፡ «ሊሆን አይችልም» «የተሳሳተ መዝገብ ይዘህ መጥተህ እንዳይሆን» «ወደ ሲዖል የሚገቡትን መዝገብ ይሆናል በስሕተት ያመጣህው» «እኛኮ አገልጋዮች ነን፤ የከበረ ስም እና ዝና ያለን፤ ስንኖርም፣ መድረክ ላይ ስንቀመጥም፣ ድሮም ልዩ ነን፤ የኛ መዝገብ ልዩ መሆን አለበት» «እስኪ ሌላ መልአክ ጥራ» ብቻ ሁሉም የመሰለውን በንዴት እና በድንጋጤ ይሰነዝር ጀመር፡፡ ሌሎች መላእክትም ሌሎች ዓይነት መዝገቦችን ይዘው መጥ ተው እያገላበጡ ፈለጉ፡፡ የነዚያ «የከበሩ አገልጋዮች» ስም ግን ሊገኝ አልቻለም፡፡


«እኛኮ የታወቅን ነን» አሉ አንድ አጥማቂ፡፡ «ሕዝብማ ያውቃችሁ ይሆናል መዝገብ ግን አያውቃችሁም» አላቸው መልአኩ፡፡ «እንዴት እኮ እንዴት? » አሉ በዋና ከተማዋ ታዋቂ የነበሩ ፓስተር፡፡ «ሊሆን አይችልም፤ ፈጽሞ ሊሆን አይችልም» አሉ አንድ ሼሕ፡፡ «የዚህን ምክንያት ማወቅ ትፈልጋላችሁ? » አለ አንዱ መልአክ፡፡ «አዎ» የሚል ኅብረ ድምጽ ተሰማ፡፡«ምክንያቱኮ ቀላል ነው፡፡ ሌሎችን መንፈሳዊ እንዲሆኑ ታስተምሩ ነበር እንጂ እናንተ መንፈሳውያን አልነበራችሁም፡፡ እናንተ ድራማ ስትሠሩ ነውኮ የኖራችሁት፡፡ መድረክ ላይ ወጥታችሁ መንፈሳዊ ድራማ ትሠሩ ነበር፡፡ ልብሳችሁ፣ንግግራችሁ፣የእጅ አጣጣላችሁ፣ ጸሎታችሁ፣ የተዋናይ ነበርኮ፡፡ የማትሆኑትን ነበር ስታስተምሩ የነበራችሁት፡፡ ለመሆኑ ለሕዝቡ የምታስተምሩትና እናንተ የምትመሩበት የሃይማኖት መጽሐፍ አንድ ነው? ወይስ ይለያያል? እናንተ የምድር ቤታችሁን በብዙ ሺ ብሮች እየገነባችሁ ሰዎች ግን ቤታቸውን ረስተው የሰማዩን ቤት ብቻ እንዲያስቡ ታስተምሩ ነበር፤ ሕዝቡን ስጡ ስጡ እያላችሁ እናንተ ግን አምጡ አምጡ ትላላችሁ፡፡ ሕዝቡን በባዶ እግሩ እያስኬዳ ችሁ እናንተ የሚሊዮኖች መኪና ትነዱ ነበር፤ ሕዝቡን እያስጾማችሁ፣ እናንተ ግን ጮማ ትቆርጡ ነበር፤ ታስተምሩት የነበረውኮ ያጠናችሁትን ቃለ ተውኔት እንጂ የምታምኑበትን እና የምትኖሩትን አይደለም፡፡እናንተኮ ግብር የማትከፍሉ ነጋድያን ነበራችሁ፡፡ እናንተ ከገዳም ወደ ከተማ ትገባላችሁ፤ ሰውን ግን ከከተማ ወደ ገዳም ትወስዳላችሁ፡፡ እርስ በርሳችሁ እንደ ውሻ እየተናከሳችሁ ለማስተማር እና ለመዘመር ሲሆን፣ ለማስመለክና ለማሰገድ ሲሆን፣ የአዞ እንባ እያነባችሁ መድረክ ላይ ትወጣላችሁ፡፡ እርስ በርሳ ችሁ ከበርሊን ግንብ የጠነከረ የመለያያ ግንብ እየገነባችሁ ሕዝቡን ግን አንድ ሁኑ፣ ተስማሙ፣ ታቻቻሉ እያላችሁ ታስተምራላችሁ፡፡


ለመሆኑ ይህ ሁሉ ፓስተር፣ሰባኪ፣ ዘማሪ፣ መነኩሴ፣ባሕታዊ፣ ዑላማ፣አሰጋጅ፣አስመላኪ፣ የእምነት አባት፣እያላት ነው ኢትዮጵያ እንዲህ ስሟ በድህነት እና በጦርነት የሚነሣው? ሙስና እና የዘመድ አሠራር፣ ጠባብነት እና ዘረኛነት፣ስግብግብነት እና ማጭበርበር፤ ክፋት እና ምቀኛነት የበዛው ይኼ ሁሉ አገልጋይ እያላት ነው? ለመሆኑ እናንተ ባትኖሩ ኖሮ ይህች ሀገር ከዚህስ የከፋስ ምን ትሆን ነበር?ለመሆኑ ተከፋፍላችሁ፣ተከፋፍላችሁ፣ተከፋፍላችሁ መጨረሻችሁ ምንድን ነው? ለመሆኑ አንድ ባትሆኑ እንኳን ለመግባባት፤ ለመገነዛዘብ፤ ቢያንስ ላለመጠላላት፤ ቢያንስ በጠላትነት ላለመተያየት፤ ላለመወጋገዝ፤ ላለመነቃቀፍ አስባችሁበት ታውቃላችሁ? የሀገራ ችሁ ፖለቲከኞች እንኳን የሥነ ምግባር ደንብ ይኑረን ሲሉ እናንተ ለመሆኑ የሥነ ምግባር ደንብ አላችሁ? ሻማ ሲበራ ዋናው ጨለማ ከሻማው ሥር ነው የሚገኘው፡፡ ሌላውን ታበራና ሻማዋ ለራሷ ጨለማ ትሆናለች፡፡ እናንተስ? በየቤተ እምነታችሁ ያለውን ችግር መቼ ፈታችሁ ነው ሕዝብ እናስተምራለን የምትሉት? ለናንተ ሁልጊዜ ጠላታችሁ ሌላ እምነት የሚከተለው ብቻ ነው? ለራሳችሁ ግን ከራሳችሁ በላይ ጠላት የለውም፡፡ ሕዝቡኮ አንዳችሁ ሌላውን ስትተቹ፤ አንዳችሁ በሌላው ስትሳለቁ፤ አንዳችሁ በሌላው ላይ ነጥብ ስታስቆጥሩ፤ አንዳችሁ የሌላውን ኃጢአት ስትዘረዝሩ መስማት ሰልችቶት ነበር፡፡


«ታድያ እኛ ያስተማርነው ሕዝብ እንዴት ጸደቀ? » የሚል አንድ ድምጽ ተሰማ፡፡ «ሕዝቡማ ምን ያድርግ በምትናገሩት እናንተ አልተጠቀማችሁም እንጂ ሕዝቡማ ተጠቀመበት፡፡ ሕዝቡማ በሁለት መንገድ ተጠቀመ፡፡ እናንተን እያየ «እንደነዚህ ከመሆን አድነን» በማለቱ ተጠቀመ፤ የምትሉትን እየመዘነ በማድረጉም ተጠቀመ፡፡ እንደ እናንተ ቢሆን ኖሮማ ማን ይተርፍ ነበር፤ አጫርሳችሁት ነበርኮ፡፡ የዚህ ሕዝብ ጉብዝናው ይሄ አይደል እንዴ፤ ሙዙን ልጦ መብላቱ፡፡ ሲገዛው ከነልጣጩ ነው፤ ሲበላው ግን ልጦ ነው፡፡ የእናንተንም ትምህርት የሰማው መላጥ ያለበትን ልጦ እየጣለ ነው፡፡እናንተ ለዚህች ሀገር መድኃኒት ነበራችሁ፡፡ ነገር ግን ጊዜው እንዳለፈበት መድኃኒት በሽታዎቿ ሆናችሁ፡፡ የሚከተል እንጂ የሚድን፤ የሚያደንቅ እንጂ የሚለወጥ፤ የሚያወቅ እንጂ የሚሠራ፣ የሚመስል እንጂ የሚሆን መች አፈራችሁ? ሕዝቡን የናንተ ተከታይ አድርጋችሁት ቀራችሁ፡፡ ያንን ጠባያችሁን ይዛችሁ እዚህ ከገባችሁ ደግሞ የገባውን ታስወጡታላቸሁ ተብሎ ይፈራል፡፡የሚያለቅሱ ድምጾች እየበረከቱ መጡ፤ አንገታቸውን ያቀረቀሩት ብዙዎች ናቸው፡፡ አንዳንዶቹን ፀፀቱ ያንገበግባቸው ነበር፡፡ ሌሎቹም ራሳቸውን ጠሉት፡፡«አሁን ምንድን ነው የሚሻለን» አሉ አንድ ፓስተር፡፡«የዚህን መልስ እኔ መስጠት አልችልም፤ ፈጣሪዬን ጠይቄ መምጣት አለብኝ» አለና መልአኩ ትቷቸው ሄደ፡፡ ከደቂቃዎች በኋላ ሲመለስ እንዲህ የሚል መልስ ይዞ ነበር፡፡«አንድ እድል ይሰጣችሁ፡፡ ትስተካከሉ እንደሆነ አንድ እድል ይሰጣችሁ፡፡ ሕዝቡን ተውትና ራሳችሁን አስተካክሉት፤ ያኔ ሕዝቡ በራሱ ጊዜ ይስተካከላል»ድንገት ሁሉም መሬት ላይ ተገኙ፡፡ እነሆ አሁን በየቤተ እምነቱ ያሉት በዚህ መንገድ የተመለሱት ናቸው፡፡

                                                                                      ምንጭ፦ ስማችሁ የለም
                                                                                               በዲ/ን ዳንኤል ክብረት 

No comments:

Post a Comment