Wednesday, June 22, 2016

ኦርቶዶክሳዊ የቅዱሳት ሥዕላት አሣሣል

ቅዱሳት ሥዕላት "ቅዱስ" እና "ሥዕላት" ከሚሉት ቃላት የተገናኘ ወይም የተሰናሰለ ቃል ሲሆን፤ሥዕል በቁሙ፣ መለክ፣ የመልክ ጥላ፣ንድፍ፣አምሳል፣ንድፍ ውኃ፣በመጽሔት፣ በጥልፍ፣በስፌት ወይም በቀለም በወረቀት ገዝፎ ተጽፎ፤ከእብን ከእፅ ከማዕድን ታንጦ፡ተቀርጦ ተሸልሞ አጊጦ የሚታይ የሚዳሰስ ነገር ነው።(ኪ.ወ.ክ፡673) ሥዕል ነጠላ ሲሆን ሥዕላት ደግሞ ብዛትን ያመለክታል።ቅዱሳት የሚለው ቃል ደግሞ "ቀደሰ" ከሚለው የግእዝ ግሥ የተወሰደ ሲሆን ትርጉሙም  ለየ፣አከበረ፣መረጠ ማለት ነው።ከዚህ በመነሳት ቅዱሳት ሥዕላት ለእግዚአብሔር የተለዩ፣የተቀደሱ፣ ልዩ፣ ምርጥ፣ንጹህና ጽሩዕይ የሆኑ የቤተመቅደሱ መገልገያ ንዋያተ ቅድሳት በመሆናቸው ቅዱሳት ተብለው ይጠራሉ።

ዳግመኛም የቅዱሳንን ታሪክና ማንነት በጊዜው ላልነበርን በመንፈስ ዓይን ፤እንድናይ ስለሚያደርጉን፤አንድም ሥጋዊውን ዓለም ከሚያንጸባርቁ ዓለምውያን ሥዕላት ፈጽመው የተለዩ በመሆናቸው፤አንድም የቅዱሳኑ ቅድስና ሥዕላቱን ቅዱስ ስላሰኛቸው፤አንድም በሥዕላቱ አድሮ እግዚአብሔር ስለሚፈጽማቸው ገቢረ ተዓምራት የተነሳ ሥዕላቱ "ቅዱሳት ሥዕላት" ተብለው ይጠራሉ።በአጠቃላይ በኢትዮዽያ ኦርቶዶክስ ተውህዶ ቤተ ክርስቲያን "ቅዱሳት ሥዕላት" ተብለው የሚጠሩት የቅዱስ እግዚአብሔር፣ የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም ፣የቅዱሳን መላእክት፣የቅዱሳን ነቢያት፣የቅዱሳን ሐዋርያትና የሌሎች ቅዱሳን ጻድቃን ማንነት ሕይወትና ታሪክ የሚያሳዩ ሥዕሎች ናቸው።ቤተክርስቲያን ሐዋርያዊት እንደመሆኗ መጠን የምትፈጽማቸው አገልግሎቶችና ሥርዓቶች ዶግማና ቀኖናን እንዲሁም ትውፊትን መሰረት ያደረጉ ናቸው።ይህ ደግሞ ኦርቶዶክሳዊያን ቅዱሳት ሥዕላት በእግዚአብሔር ፈቃድ ሐዋርያዊ ቀኖናን ተከትለው የሚሳሉ የቤትክርስቲያን ንዋያተ ቅዱሳት ናቸው እንጂ እንዴው በዘፈቀደ የሚዘጋጁ የኪነጥበብ ስራወች አለመሆናቸውን ያስገነዝባል።

የቤተክርስቲያንን ሥላት ልዩ ከሚያደርጓቸው ገጽታወች መካከል አንዱ ትምህርተ ሃይማኖትን ጠብቀው መሳላቸ ነው።ዓላማቸው ወንጌልን ለመስበክ ለማስተማሪያነት ስለሆነ ሰፊውን ትምህርተ ሃይማኖት በሥዕል የሚገልጡ መሆን አለባቸው።ትምምህርተ ሃይማኖትን ያልጠበቁ ሥዕላት ከሆኑ ግን የሚያስተምሩት ትምህርት ኑፋቄ ስለሚሆን ቤተክርስቲያን አትቀበላቸውም።ለምሳሌ ቅድስት ሥልሴ ሲሳሉ አንድነታቸውና ሦስትነታቸው በሥዕል ይገለጣል።አንድነታቸውን ለመግለጽ ነደ እሣት የሚሆኑ ኪሩቤል በተሸከሙት አንድ መንበር እንደተቀመጡ ልብሳቸው ሳይነጣጠል፤ሦስትነታቸውን ዓለምን በቀኝ እጃቸው እንደያዙ ፣የሦስቱም ፊት ወደ አንድ አቅጣጫ እየተመለከቱ አካላቸው ገጽታቸው በተመጣጣኝ ሁኔታ ይሣላል። የጌታ ትንሳኤ ሲሳል መግነዝ ፍቱልኝ መቃብር ክፈቱልኝ አለማለቱን ለመግለፅ የተዘጋ መቅብር ይታያል።በትንሳኤው ብርሃን ዓለምን የቀደሰ ነውና  ብርሃን ጨለማውን ሲገልጥ የሚያሳይ ተደርጎ ይሳላል።ሆኖም ግን በአንዳንድ የምዕራባውያን አብያተ ክርስቲያናት ሥዕላት ላይ የምንመለከተው የተከፈተ መቃብር ወይም መላእክት የመቃብሩን በር ለጌታችን ሲከፍቱለት የሚያሳይ ሥዕል ነው።ይህም በስልጣኑ አልተነሳም የሚል ትርጓሜን ይሰጣል።ይህ ደግሞ ትምህርተ ሃይማኖትን ስለሚፋልስ ቤተክርስቲያን አትቀበለውም።

በኢትዮዽያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርቲያን ቀኖና መሰረት የቤተክርስቲያን ቅዱሳት ሥዕላት መልክና ቁመና ሲሣሉ ራሱን የቻለ ህግና ሥርዓት አለው።ቅዱሳት ሥላት ሲሣሉ በገሀዱ ዓለም የተለመደውን (realistic) የአሣሣል ዘይቤ አይከተሉም።ምክንያቱም የሥዕላቱ ዓለማ መንፈሳዊነትን መግለፅና ውክልና(religious symbols)እንጂ እውነተኛ መልካቸው እንዲህ ነው ለማለት ስለማይሳል ነው።የሚከብሩት በነፍሳቸው ባገኙት ክብር እንጂ በሥጋቸው ግዝፈትና ርቀት አይድለምና ።ከዚህ በተጨማሪ ጠይም፣ ጥቁር፣ ነጭ፣ቀይ፣ረጅም፣አጭር፣ወፍራም ወይም ቀጭን ወዘተ በሚለው ላይም አያተኩሩም።የቅዱሳት ሥዕላት ፊት ሲሳል  ሰፊና ክብ ተድርጎ ይሳላል።ሰፊና ክብ መሆኑ የፍጹምነት ምሳሌ አንድም መላ ሕይወታቸውን ለጽሎትና ለተመስጦ እንዳዋሉ ለመግለጽ ነው።ትልቅ፣ክብና ሰፊ ተደርገው መሳላቸው ለውክልና እንጂ ይህንን ይመስላሉ ለማለት ግን አይደለም።

ቅዱሳት ሲሣሉ ዓይናቸው ጎላጎላ ተደርጎ ይሣላል።ጎላ ጎላ ማለቱ ክፉውን ከደጉ፣ጨለማውን ከብርሃኑ ለይተው በተቀደሰው ጎዳና  በፍጹም አስተዋይ ልቡና የተጓዙ መሆናቸውን ለማመልከት፤አንድም ሥጋዊውንና መንፈሳዊውን ፣ረቂቁንና ግዙፉን ዓለም በግልፅ የማየት ጸጋ እንዲሁም ከሰው ልጆች ሕሊንና አእምሮ በላይ የሆነውን ረቂቅ መለኮታዊ ምስጢር በስፋት በማወቅ አቅምና ጣዕሙን የመረዳት ችሎታ ከቸሩ አምላክ በልግስና እንደተሰጣቸው እናስተውላለን።ከዚህ በተጨማሪ ዓይናቸው ጎላ ጎላ ማለቱ የተመልካቹን ምዕመን ልብ ለመሳብ፣ለመመሰጥ፣የመደመምን ስሜትና ፈሪሃ እግዚአብሔርን ለመፍጠር ይጠቅማል።ዓይኖቻቸው የሚያዩትም ወድ አንድ አቅጣጫ ብቻ ነው ።ይህም አንዲት መንግስተ ሰማያትን በአይነ ህሊና በመመልከት ለክብር እንደበቁ ለማመልከት ነው።ዳግመኛም አንዲት ርትዕት ኦርቶዶክስ ተውህዶ ሃይማኖትን ሳይፈሩና ሳያፍሩ ያለ ጥርጥር ተቀብለውና መስክረው የኖሩ መሆንቸው እንዲሁም ጥርጥር በልባቸው አለመኖሩን ያጠይቃል።የተረዳች የቀናች ሃይማኖትን ጥብቀው ያስጠበቁ በክብር  ወደ ዘላለም ርስት ያቀኑ በመሆናቸው ወደ አንድ አቅጣጫ እየተመለከቱ ይሳላሉ።ዓይን የሰውነት መብራት ናት እንዲል።(ማቴ 6፡22)

በሥዕሉ ባለቤት ራስ ዙሪያ ላይ የምንመለከተው ጸዳለ ብርሃን (አክሊለ ብርሃን) ደግሞ ቤበተክርስቲያናችን የቅድስና ማዕረግ እንደተሰጣቸው ያጠይቃል።ነገር ግን በቅድስት ስላሴና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ላይ የሚደረገው ፀዳለ ብርሃን የእግዚአብሔር ቅድስና የባህርይው መሆኑን እንደሚገልፅ መረዳት ያስፈልጋል።እኔ እግዚአብሔር አምልካችሁ ቅዱስ ነኝና እናንተም ቅዱሳን ሁኑ እንዲል። (ዘሌ 19፡2፣ 1ዼጥ 1፡15-16)  በአጠቃላይ ሥዕሎቻችን በኪነ ጥበብ ዘርፍ የተለመደውን የተከያዩ ህዋሳተ አካልን ትክክለኛ መጠን ላይጠብቁ ይችላሉ።ይህ የሚሆነው  ደግሞ ሥዕላቱ ውክልና ሃይማኖታዊ ምልክቶች በመሆናቸው፤አንድም ሥዕላቱ የሚሳሉት ቅዱሳን ይህንን ይመስላሉ ይህንን ያክላሉ ለማለት አይደለምና ፤አንድም የሚያስተዋዉቁን ከመንፈሳዊው ዓለምና ጣዕመ ጻጋ ጋር እንጂ ከምድራዊው ዓለም ጋር ባለመሆኑ ነው።በመሆኑም በቅዱሳት ሥዕላቱ ላይ ሊተላለፍ የተፈለገውን  ልዩና ጥልቅ መንፈሳዊ መልክእክት በመረዳት ተገቢውን አክብሮት መስጠት ይገባል።

በቤተክርስቲያናችን ቀኖና መሰረት አብዛኛውን ጊዜ የምንጠቀማቸው ቀለማት፦ ሰማያዊ፣ቀይ፣አርንጓዴ፣ቢጫና ነጭ ሲሆኑ ቀለማቱ ራሱን  የቻለ ምስጢር ወይም ትርጉም አላቸው ።

1) ሰማያዊ፦ሰማያዊውን ሃብት ግነዘብ ለማድረግ በፈቃደ ነፍስ መመራትን ለማመልከት እንዲሁም በመንፈስ ፍሬወች ፈቃደ ሥጋን በፈቃደ ነፍስ ድል ማድረጋቸውን፤አንድም ትህትናን ያሳያል። ቅዱሳን በትሕትና ለመኖራቸው ማሳያ ነው ።በመሆኑም ይህ ቀለም መንፈሳችን በእምነት መንገድና በትህትና  የመንፈስ ፍሬዎችን ገንዘብ በማድረግ እንድንጓዝ ያስታውሰናል።

2)ቀይ፦ሰማዕትነትን ያሳያል።ይህም ቅዱሳን ነፍሳቸውን ለመከራና ለሞት አሳልፈው ስለክርስቶስና ስለቤተክርስቲያን ብለው መስጠታቸውን ለማመልከት ይህን ቀለም እንጠቀመዋለን።የመስዋዕትነት የነፃ አውጭነት ምልክት ነው።ጌታችን በሸንጎ ፊት ቆሞ የለበሰው ልብስ ቀይ ሐር እንደነበር።(ማር 15፡16-17፣ ኢያ2፡18)

 3)ቢጫ ፦ይህ ቀለም እውነተኛነትንና ብርሃንነትን ይገልፃል።እናንተ የዓለም ብርሃን ናችሁ እንዲል (ማቴ5፡14)። ከዚህ በመነሳት ቤተክርስቲያን የቅድስና ማዕረግ ላይ የደረሱትን ቅዱሳት እውነተኞችና የዓለም ብርሃን ናችሁ ስትል በራሳቸው የብርሃን አክሊል በቢጫ አድርጋ  ትሥላለች።

4)አረንጓዴ፦ከልምላሜ ከፀደይ ጋር ስለሚያያዝ መንፈስዊ ትርጉሙ መታደስን አዲስ ሕይወትን፣ድህነትንና ተስፋን ያሳያል።በዚህ መሰረት አረንጓዴነትና ሕይወት ተወራራሽ ይሆናሉ።

5)ነጭ፦የድል አድራጊነት የንፅህና እና የፍጹምነት ምሳሌ ነው።ቅዱሳን ዓለምንና ምኞቱን ድል ያደረጉ ልበ ንጹሃን በመሆናቸው ነጭ ልብስ ለብሰው ይሳላሉ።ነጭ ልብስ ለብሰዋል ፤ከአለቆቹም አንዱ "እነዚህ ነጫጭ የለበሱት እነማን ናቸው? ከየት መጡ?" አለኝ።እኔም "አቤቱ አንተ ታውቃለህ" አልኩት። እርሱም "እሊህ ከጽኑ መከራ ነጻ የወጡ ልብሳቸውንም በበጉ ደም አጥበው ያነጹ ናቸው።"አለኝ። መለኮታዊ ክብርንም ያሳያል።ለምሳሌ በደብረታቦርና በትንሳኤ ሥዕሎች ላይ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነጭ ልብስ ለብሶ ይሣላል።

በትውፊታዊ አሣሣል ቅዱሳት ሥዕላት ድርሰት ላይ የቅዱሳኑ አቋማቸው (በሥዕሉ ላይ የሚገኝበት ሥፍራ)የተወሰነ ነው።ለምሳሌ የስነ ስቅለት ሥዕል ከሆነ ጌታችን ቀይ ግልድም አድርጎ፤አንገቱን ወደ ቀኝ አዘንብሎ፤አክሊሊ ሦክ እንደደፋ፤በቀኙ እመቤታችን በግራው ቅዱስ ዮሐንስ ወንጌላዊ ሆነው።በእግረ መስቀሉ አፅመ አዳም እንዲታይ ተደርጎ ይሣላል። ምስለ ፍቁር ወልዳ ከሆነ ደግሞ እመቤታችን ጌታን ታቅፋ ከተሳለች በኋላ በግራ በቀኝ ቅዱስ ገብር ኤልና ቅዱስ ሚካኤል ይሣላሉ።ሆኖም ግን ይህ ሁሉም የሥዕል ድርሰት ላይ የቅዱሳን አቋማቸው የተወሰነ ነው  ማለት ግን አይደለም።ስለዚህ ቅዱሳት ሥዕላት ከላይ የተጠቀሱትን ቀኖናን ተከትለው  ይሣሉ ዘንድ ይገባል።

እይንዳንዱ ምዕመንም የራሱ የሆነውን ትምህርተ ሃይማኖትን ታሪክንና ትውፊትን የጠበቁትን ሥዕላት ማወቅና መረዳት ይኖርበታል።ያወቀውን ደግሞ ላላወቁት በማሳወቅ አባቶች ያስቀመጡት ድንበር እንዳይደፈር መጠበቅ ይኖርበታል። የቀደሙት አባቶች የሰሩትን ድንበር አታፍርስ እንዲል ምሳ 22፡28።


ምንጭ፦ ኦርቶዶክሳዊ ቅዱሳት ሥዕላት
አዘጋጅ፦ኃይለማርያም ሽመልስ ካሳ

No comments:

Post a Comment