Thursday, April 23, 2020

...ፍረደን...

ስማኝማ አንድዬ
ስድስት ሺህ ጅራፍ ተቆጥሮ የማያልቅ ስፍር የለሽ በደል
ለከፈልክባት ቀን እንኳን አደረሰህ አይባልም አይደል
.
የሰማዕታት ሀገር የፃድቃን ከተማ
ፅርሐዓርያም እንዴት ነው በበዓል ዋዜማ
ከዙፋንህ ግርጌ ቄጤማ ጎዝጉዘው እያሸበሸቡ
ሰውና መላእክት በአንድ ሲሰባሰቡ
ከመላእክት ምግብ ፃድቃን ሲመገቡ
ሰማይ ቤት እንዴት ነው የበዓል ድባቡ
.
ትዝ ይልሀል አይደል ?
አልጋውን አስይዘህ ያ'ዘለልከው ድኩም
አላውቀውም ብሎ የመታህ በኩርኩም
እንዴት ነው መፃጉ ኑሮ እንዴት ይዞታል
ቸርነትህ ደርሶት እርሱም ገነት ገብቷል
ወይስ የሲዖል ፍም እሣት ተስማምቶታል
.
ኑሮ ከተባለ እኛ አለን እንዳለን
አንተን መስለንና ያንተን አስመስለን
እንደ ኮሶ እንደ ሬት ኑሮ እየመረረን
እኔን ምሰሉ ሚል ቃልህን አክብረን
ሰውን ያክል ክቡር ነፍስ ተሸክመን
ፈውስ ያልተገኘለት new virus አክመን
አድናለሁ ስንል እራሳችን ታመን
.
ሰርዷችንን ግጦ የጠገበ ኮርማ ዞሮ እየረገጠን
ወርቅ የሰፈርንለት አመድና ትቢያ አፈር እየሰጠን
ኑሮ ከተባለ እኛ አለን እንዳለን
አንተን መሆን ባንችል ያንተን አስመስለን
.
እናልህ አንድዬ
እንዳይጎርስ ለጉመው እንዳይሄድ ቀይደው
ቤቱ  እንዳይቀመጥ በሥራ ጥመደው
የሚል ህግና ደንብ ከልካይ አዋጅ ወጥቶ
ተመጥምጦ አለቀ ጉልበታችን ሟሙቶ
.
በራሳቸው ችሎት
ራሳቸው ከሳሽ ራሳቸው ዳኛ ሆነው እየቀጡን
ውኃ ጠማን ስንል ሆምጣጤ እያጠጡን
ከኩንታል ሙሉ ማር ሸክማችን ከበደ
ወዳንተ እንዳንመጣ ጉልበታችን ራደ
እንደ ልባሽ ጋቢ ዋጋችን ቀለለ
እባክህ ቶሎ ና ትክሻችን ዛለ
.
ልብሳችንን ነክተው ደማቸው ቀጥ ያለ ከሞት የተረፉ
ሀኪም ድሮ ቀረ እያሉ ለፈፉ
በእኛ መስዋዕትነት ከመቅሰፍት የዳኑ
በፈውሳቸው ማግስት እኛ ላይ ጀገኑ
 .
መንግሥት!?
መንግሥትማ አለ እንጅ ስራውን ይሰራል
ዘላለም የመንገሥ መብቱን ያስከብራል
የተቃዋሚውን ጀርባ አጥንት ይሰብራል
በጠብመንጃው አረር የደቀቁ እግሮችን ሆስፒታል
ይልካል
እንቶኔና እንትና በፈጠሩት ግጭት እያለ ይሰብካል
.
ተሰባሪው ታዲያ ሰባሪውን ፈርቶ አዳኙን ይከ'ሳል
የሀኪሞች ስህተት ውጤት ነው እያል አቧራ ያስነሳል
በርግጥ ሰው ይስታል እውነቱ አይካድም
በማካሮ ሽጉጥ መስበሩ ባይከብድም
ለዜና ካልሆነ
የተሰበረ እግር በጥገናው ማግሥት ቆሞ አይራመድም
.
እናልህ አንድዬ
በዚች የጉድ ሀገር ባልታደለ ዘመን በጉድ ወቅት ተፈጥረን
አንድ ቀን ከግማሽ ያለምንም ዋጋ ዱቲ ተወጥረን
ሥራ አጥ በሚል ማዕረግ ኩንትራት ተቀጥረን
በእለተ ትንሳኤ ላባችን ገብረን በደማችን ሰክረን
ካሣ' ሙሉ ፈጅቶ የመጣ ሰካራም እያደነቆረን
ልዝብ ያልከው ቀንበር ሸክሙ ከበደን
ነፃ አውጭ ላክልን ወይ መጥተህ ፍረደን
.
 (መታሰቢያነቱ፦ የትንሳኤ በዓልን ከቤተሰብ ተለይታችሁ ሆስፒታል ውስጥ ለምታሳልፉ የጤና ባለሙያዎች በተለይ በአውደ ዓመት ምድር ያለምንም ክፍያ ላብና ደማችሁን ለምትገብሩ ኢንተርን ሀኪሞች እንዲሁም ምንም ነገር ባልተሟላበት ሁኔታ ከኮሮና ቫይረስ ጋር ለምትዋጉ የጤና አርበኞች ይሁንልኝ ።)