Wednesday, September 04, 2024

በልብስ ወበሢሳይ ኢታርእዪኒ ንዴተ

 በልብስ ወበሢሳይ ኢታርእዪኒ ንዴተ

እስመ ቁር ወረኃብ ያረስእ ጥበባተ
በአፄ ምኒልክ ዘመን አለቃ ተክሌ የሚባል የንጉሥ ተክለኃይማኖት አሽከር በአፈ ንጉሥ ይግዛው ስም የተንኮል ማህተም ቀርጠኻል በሚል ተወንጅሎ እስር ይፈረድበታል። ወህኒ ቤት በገባ ጊዜም "ስለ እግዚአብሔር ብለው አይርሱኝ፤ ለጃንሆይ ያስተዛዝኑልኝ፤ ዘመድ የለኝም"ብሎ አሳላፊ ውቤን ወደ እጨጌ ወልጊዮርጊስ ላከ። አለቃ ተክሌ ወህኒ ቤት ሳለ መልክአ ኤዶም ይደግም ነበረ። ያን ጊዜም ከበጅሮንድ ገድሌ ቤት ታሥሮ የተቀመጠው አለቃ ተገኝ "ወረድኦ ለነዳይ በተጽናሰ (ችግረኛውን በችግሩ ጊዜ ረዳው)" የሚል ሕልም ስለ አለቃ ተክሌ አየ።
አለቃ ተክሌ መልክአ ኤዶም እየደገመ ባዘነበት የሰኔ ማርያም እለት እጨጌ ወልደ ጊዮርጊስ ለእቴጌ ጣይቱ ነገረለት። እቴጌ ጣይቱም "ለጃንሆይ ነግሬ አስፈታዋለሁ፤ ጉራምባ ማርያምን ይሥልልኛል" አለች። ከዚያም " አለቃ ተክሌን ፈተው ለእኔ ይስጡኝ፤ ጉራምባን ይሣልልኝ፤ በሎልነቱ ታዝዞ ማኅተም ቢሰራ በርሱ ምን ኃጢአት አለበት ?" አለችና ለጃንሆይ ተናገረች። እጨጌ ወልደጊዮርጊስም አከታትሎ አስተዛዘነለት ።አፄ ምኒልክም "እሽ ይፈታ" አለ።
ለአማኑኤል ተስሎ ቀሚሱን በሰጠበት ሰኔ ፳፰ ቀን የአማኑኤል ዕለት ከወህኒ ቤት ወጣ። ከተፈታ በኋላ ለእቴጌ ሹም ለአዛዥ
ዘአማኑኤል ተላለፈ። አዛዥ ዘአማኑኤልም ራት ምሣውን፣ ምንጣፍ ሥፍራውን አዘዘለትና በማዕረግ ተቀመጠ። ነሐሴ ፪ ቀን እቴጌ ጣይቱ ሙያውን ልትሰልል "ሥዕለ ማርያም በወረቀት ሥለህ ስደድልኝ" ብላ ላከችበት። እርሱም ፩ ሉክ ወረቀት ተቀብሎ ጥሩ ሥዕል ሥሎ ከሥዕሉ ግርጌ
ኢትኀድግኒ ዓቂበ
በልብስ ወበሢሳይ ኢታርእዪኒ ንዴተ
እስመ ቁር ወረኃብ ያረስእ ጥበባተ
[መጠበቅን አትተይኝ
በልብስና በምግብ ችግር አታሳይኝ። ብርድና ረሃብ ጥበብን ያስረሳልና።] የሚል ጽሑፍ ጽፎ ሰደደላት።
እቴጌ ጣይቱም ሥዕሉን አይታ አደነቀች ፤ለጃንሆይም አሳየች ። ከሥዕሉ ግርጌ ያለውን ጽሑፍ ባየች ጊዜ አዛዥ ዘአማኑኤልን ተቆጣች። "ካላስራብኸው እንዲህ ብሎ አይልክም" አለች። አዛዥ ዘአማኑኤልም ከመጣ እስከ ዛሬ ድርጎው አልገደለበትም። "እንዲያው ጎጃሞች ልፍ(ማሳጣት፣ክስ) ይወዳሉ "አለና አለቃ ተክሌን ተጣላው። እቴጌ ጣይቱ ግን የሰርክ ልብስ፣የሌሊት ቡልኮ፣ ለቀን ጥበብ ኩታ፣ እጀ ጠባብና ሱሪ በርኖስ ዳረገችው። ነሐሴ ሲያልቅ ጳጉሜ ፫ ቀን ጉራምባን ይሣል ብላ ፫ ዳውላ እህል ቀለብ፣ ፪ ጉንዶ ማር፣ ለወር ፩ ሙክት፣ ለ ፲ ቀን ፭ ኩባያ አሻቦ፣ ፩ እቃ ቅቤ፣ ጾም ቢሆን ቅባኑግ ለወር ዳረገችው። የቀለም መበጥበጫ ፲፪ ፍንጃል አዘዘች።
ኢትኀድጉኒ ዓቂበ
በልብስ ወበሢሳይ ኢታርእዩኒ ንዴተ
እስመ ቁር ወረኃብ ያረስእ ጥበባተ
[መጠበቅን አትተውኝ
በልብስና በምግብ ችግር አታሳዩኝ። ብርድና ረሃብ ጥበብን ያስረሳልና።]


ፍኖተሰላም ሆስፒታልን ከልጅነቴ ጀምሮ አውቀዋለሁ።




ፍኖተሰላም ሆስፒታልን ከልጅነቴ ጀምሮ አውቀዋለሁ።

የታመመ ሰው ህክምና ለማግኘት ጥዋት 11 ሰዓት ላይ ከሆስፒታሉ ግቢ ውጭ ነበር ወረፋ የሚይዘው (ይሰለፋል)። ወይም ወረፋ ከሚይዙ ወጣቶች መግዛት ይጠበቅበታል (ከተሜ ከሆንህ ነው)።
እድለኛ ከሆነና ከውራጌወች ካመለጠ ፣ ከብዙ ስቃይ በኋላ ወደ ሆስፒታሉ ቅጥር ግቢ ውስጥ እንዲገባ ይፈቀድለታል። እድለቢስ ከሆነ ደግሞ በተረገሙ ውራጌወች ተደብድቦ ገንዘቡንና ስንቁን ይቀማል (ህክምና ሲመጣ ስንቅ ተይዞ ነበር የሚመጣው ቢያንስ ለሳምንት የሚሆን፣ ክብ ዳቦ፣ ዳቦ ቆሎ፣ በሶ)። አልያም ለቀጣይ ቀን ይቀጠራል።
ከሆስፒታሉ አጥር ውስጥ ሳይገባም ህይወቱ የሚያልፍ ብዙ ታካሚ ነበረ። ሀኪም አግኝቶ ታክሞ ከተሻለው ፣ ተንበርክኮ መሬት ስሞ ፣ አገር ይባረክ ፣ ወንዝ ይባረክ፣ አገራችን ኢትዮጽያን ይጠብቅልን፣ ገበያውን ጥጋብ ያርገው፣ በእውቀት ላይ እውቀት ደርቦ ይስጥህ ብሎ ከልቡ መርቆ ይሄዳል።
ካልተሳካ ደግሞ ወደ ባህርዳር ወይም ደብረማርቆስ ሪፈር የሚባለው ታካሚ በጣም ብዙ ነበር (ወደ ከፍተኛ ተብሏል ፣ ግልኮስ ተደርጎበታል፣ ህመሙ ሳይጠናበት አልቀረም፣ ኧረ እኔስ ፈርቻለሁ አይመለስም ፣ይባል ነበር) ።
ያን ሁሉ መከራ ግን ዛሬም አልቀረም ፣ ብዙ ነገሮች በተሻሻሉበት ዘመን ፣ ወንበር ላይ ተቀምጦ ኦክስጅን ይወስዳል፣ ፈጥኖ የመጣና እድለኛ ከሆነ ደግሞ የጎኑ ማሳረፊያ ደረቅ ወንበር ያገኛል፣ አልያም ፍሳሽ የሚወርድበት ክፍል ውስጥ የዛገ አልጋ ላይ ጣል የተደረገች ብል የበላት ፍራሽ ትሰጠዋለች።
አካባቢው የተማሩ ልጆች እያሉት፣ እያመረተና እየገበረ ምን ስላደረገ ነው ይህ ማህበረሰብ በዚህ ልክ የሚሰቃየው! ተማርን የምንል ሰዎች፣ ነጋዴዎች እና ባለስልጣናት የማህበረሰቡ ህመም ሊያመን ይገባል።
ለዚሁ ዓላማ ብቻ የተከፈተውን የ telegram group ይቀላቀሉ።
NB: "ውራጌ" ማለት በአካባቢው ዘዬ ሌባ ፣ ነጣቂ ፣ ቀማኛ፣ ዘራፊ ማለት ነው
ዶ/ር የሮም ጌታቸው የፍ/ሰላም ሆስፒታል ሜዲካል ዳይሬክተር

ኑ! ሆስፒታሉን ሆስፒታል እናስመስል

ግርማዊነታቸው ከጣሊያን ጦርነት በኋላ ከስደት ወደ ኢትዮጵያ ሲመለሱ የጎጃም እምብርት ላይ በምትገኝና ወጀት ተብላ በምትጠራ ትንሽዬ ከተማ ላይ ከአጃቢዎቻቸው ጋር እረፍት ያደርጋሉ። እስከዚያን ጊዜ ድረስ ያደረጉት ጉዞ በሰላም የተሞላ ነበርና ከተማዋን ፍኖተ ሰላም ብለው ሰየሟት። የሰላም መንገድ ማለታቸው ነው፡፡ ከከተማዋ ወጣ ብለውም ለማስታወሻ ይሆን ዘንድ አንድ ዋርካ ተከሉ።

ጃንሆይ በቆይታቸው ሰው ሰው አክባሪ፤ወዲህ እንግዳ ተቀባይ፤ አካባቢው ጤፍ፣ በቆሎ፣ ዳጉሳ፣ ኑግ፣ በርበሬ እና ሌሎችንም የእህል አይነቶች የሚያበቅል፤ ሎሚ፣ ብርቱካንና ፓፓዬ እንደልብ የሚግኝበት፤ በተፈጥሮ ለምነትን የታደለ፤ መሆኑን አስተዋሉ። የባከልን ቡና ቀምሰውም በጣዕሙ ተደመሙ። ጃንሆይ ምልከታቸው በዚህ አላበቃም፡፡ የአካባቢው ህዝብ በስጋ ደዌና በቲቪ በሽታ እንደሚሰቃይ አይተው አውጥተውና አውርደው ሆስፒታል አስገነቡለት፡፡
ከ62 ዓመታት በፊት ቲቢና ስጋ ደዌ በሽታን ለማከም ታስቦና አብዛኛው ወጪው በህዝቡ ተሸፍኖ የተገነባው ፍ/ሠላም ሆስፒታል በ1976 ዓ.ም በከፍተኛ የአካባቢዉ ማህበረሰብ ተሳትፎ ማስፋፊያ ተደርጎለት በገጠር ሆስፒታል ደረጃ ለማደግ የቻለ ሲሆን፤ ከ2012 ዓ.ም ጀምሮ ወደ ጠቅላላ ሆስፒታልነት በክልሉ ጤና ጥበቃ ቢሮ ለማደግ ችሏል፡፡ ተቋሙ 297 የጤና ባለሟያዎች እና 102 የአስተዳደር ሰራተኞች በድምሩ 399 ቋሚ ተቀጣሪ ሰራተኞችን ይዞ ለአካባቢው ማህብረሰብ አገልግሎት በመስጠት ላይ ይግኛል፡፡
በ2016 ዓ.ም 88,230 የተመላላሽ ታካሚዎችን ፣5,704 ተኝቶ ታካሚዎችን ፣ 11,462 የድንገተኛ ክፍል ታካሚዎችን፣3,479 የወሊድ አገልግሎት፣1,754 ከፍተኛ ቀዶ ጥገና ስራዎችን እና ሌሎች ዘርፈ ብዙ የሆስፒታል አገልግሎቶችን ሲሰጥ የከረመ ሲሆን በአሁኑ ሰዓት በቀን 400-600 ህሙማንን እያስተናገደ ይገኛል፡፡ ሆስፒታሉ በስሩ አምስት የመጀመሪያ ደረጃ ሆስፒታሎች ማለትም( ፈረስ ቤት የመጀመሪያ ደረጃ ሆስፒታል፣ደምበጫ የመጀመሪያ ደረጃ ሆስፒታል ፣ቡሬ የመጀመሪያ ደረጃ ሆስፒታል ፣ዱርቤቴ የመጀመሪያ ደረጃ ሆስፒታል ፣ሊበን የመጀመሪያ ደረጃ ሆስፒታል) እንዲሁም ሶስት የከተማ ጤና ጣቢያዎችን( ቋሪት ጤና አጠባበቅ ጣቢያ፣ ጅጋ ጤና አጠባበቅ ጣቢያ ፣ፍ/ ሰላም ጤና አጠባበቅ ጣቢያ) በስሩ በክላትተር ትስስር ይዞ በመስራት ላይ ይገኛል፡፡
ይሁን እንጅ ይህ የእድሜ ባለጸጋ ሆስፒታል ከአቻዎቹ ጋር እኩል ማደግና ዘመኑን የዋጀ እንዲሁም ያለውን የታካሚ ፍሰት የሚመጥን አገልግሎት መስጠት ባለመቻሉ በተደጋጋሚ ቅሬታዎች ይነሱበታል። በቅርቡ ባዲስ መልክ የተዋቀረው የሆስፒታሉ ማኔጅመንት ይህንን ችግር ለመፍታት ኮሚቴ አቋቁሞ በመንቀሳቀስ ላይ ይገኛል፡፡ ኮሚቴውም ሆስፒታሉ የሚጠበቅበትን አገልግሎት በአግባቡ እንዳይሰጥ ማነቆ የሆኑበትን ችግሮች በመለዬት እንደ ችግሩ ስፋትና ክፋት በቅደም ተከተል ለመፍታት ደፋ ቀና በማለት ላይ ነው፡፡
ስለሆነም የፍኖተሰላም ከተማና አካባቢው ነዋሪዎች፣ተወልጆች፣ባልሃብቶች፣አዋቂና ታዋቂ ሰዎች፣የሚመለከታችሁ የመንግስት አካላት፣መንግስታዊና መንግስታዊ ያልሆናችሁ ድርጅቶች ሆስፒታሉን ሆስፒታል ለማስምሰል በምናደርገው እንቅስቃሴ ሁሉ ተቋሙን እንደ ራሳችሁ ቤት ቆጥራችሁ ከጎናችን እንድትቆሙ ስንል በአክብሮት እንጠይቃለን፡፡
ለዚሁ ዓላማ ብቻ የተከፈተውን የtelegram group ይቀላቀሉ