Saturday, July 23, 2016

አበጀ በለው(2)

የእግዚአብሔር ዳኝነት የእግዚአብሔር እውነት፣
የሚጠበቅበት የድሆቹ መብት፣
እጅና እግሩን ታስሮ በግፍ ሰንሰለት፣
ያለ አንድ ጠበቃ ያለ አንድ ረዳት፣
ፍርድ ለመቀበል ቀርቦ ፍርድ ቤት፣
በቀማኞችና በሌቦች ችሎት፣
ይሙት በቃ ብለው ሁሉም በአንድነት፣
የአመፅ ፍርድ ፈርደው ገድለው ሲቀብሩት፤
ይህን ግፍ አዬና አበጀም አስተውሎ፣
በጦር እንደወጉት ልቡ ባዘን ቆስሎ፣
መንፈሱ በቁጣ እንደ እሣት ተቃጥሎ፣
የእውነትን ደመኞች ለመበቀል ብሎ፣
ወረደ በረሃ ቤት ንብረቱን ጥሎ።
ዳኞች ዳኝነትን ከቀበሩት ገድለው፣
የእግዜርን አደራ እምነቱን አጉድለው፣
የሰጠናቸውን ስልጣን ተከልለው፣
እኛኑ ሲያጠቁን ጠባቂዎች መስለው፣
መቀማት ሲመርጡ  መጠበቁን ጥለው፣
ካሾች እኛ ስንሆን እነሱ በድለው፣
አርደው ሲጨርሱን አንድ በአንድ አናጥለው፣
እንደ ቧዘዘ ከብት ጠባቂ እንደሌለው፣
ለመብት ሲከላከል ሊሞት እንደማለው፣
እንደ ቆራጡ ወንድ እንደ አበጀ በለው፣
እኛስ ለመብታችን የማንታገለው ፣
ከጅልነት በቀር ምን ምክንያት አለው?
የመበታችን ፋና የአርነትን ጮራ፣
የሚለይበትን ሰው ከእንስሳ ተራ ፣
ከፍ አድርጎ ይዞ ሲሄድ እያበራ፣
በነሴ በረሃ በጎንቻ ተራራ፣
ግፈኞች ከበውት ከቀኝ ከግራ፣
ቀን ከሌት ሲያድኑት ወንጀል እንደ ሰራ፣
ለምቾቱ አያስብ ለህይወቱ አይፈራ፣
እንደ አምላክ ስለሰው ሲቀበል መከራ፣
መሄዳችን ላይቀር ነገ ስንጠራ፣
ወደ ማንቀርበት ወደ ሙታን ስፍራ፣
የበሉትን ቀጥቶ የጊዜን አደራ፣
የማይቀረውን ሞት መሞት ከእርሱ ጋራ፣
የሚያጸድቅ ነበር ወዲያው የሚያኮራ።

ምንጭ፦ፍቅር እስከ መቃብር 

No comments:

Post a Comment