Wednesday, November 16, 2016

ፍቅር፣ወጣትነትና መንፈሳዊነት

ብዙ ወጣቶች በጋራ የሚያውቋቸው ዘወተር የሚነጋገሩባቸው ሕይወታቸውን እስከመለወጥ የሚደርሱባቸው ብዙ ነገሮች አሉ። ከእንዚህ ነገሮች መካከል ከተቃራኒ ጾታ ጋር ያላቸው ግንኙነት አንዱ ነው ።ይህ በእድሚያቸውና በተፈጥሮአዊ ለውጣቸው ምክንያት የሚመጣ ጠባይ በመሆኑ ወጣቶቹ መንፈሳውያን ሆኑም አልሆኑ የዚህ ነገር ተጋሪዎች ናቸው ።ለአቅመ ሔዋንና ለአቅመ ዓዳም ከደረሱበት ጊዜ አንስቶ አስተሳስባቸውና አመለካከታቸው ፣በትምህርት ቤትም ሆነ በሥራ ከሚያገኟቸው በጾታ ተቃራኒዎቻቸው ከሆኑት ጋር ያላቸው ጉድኝት እንደ ሕፃንነቱ ወቅት አይሆንም ።ራሳቸውን ይመረምራሉ።እነርሱ ስላልደረሱበት ነገር ለማወቅ ያላቸው ጉጉት ይጨምራል።በሚያነቧቸው መጽሔቶች፣ ጋዜጦች፣ መጽሐፍት፤በሚመለከቷቸው ፊልሞችና ድራማዎች በየመንገዶች ከሚያዩዋቸው ነገሮች በመነሳት እነርሱም ያንን የሚያደርጉበትን ቀን ይናፍቃሉ ።ይህ ናፍቆትና ፍላጎትም ያድግና በተግባር ይተረጎማል።በዚህም መክን ያት የብዙ ወጣቶች ሕይዎት ሊበላሽ ይችላል።

በሃገራችንም ሆነ በየሰንበት ትምህርት ቤቶቻችን ወጣቶች ከተቃራኒዎች ጋር ሊኖራቸው ስለሚገባው ግንኙነት ለማወቅ የሚችሉባቸው አጋጣሚዎች ብዙ የሉም።በግልፅ ሊያውቋቸው የሚገቡ  ነገሮች በነውርነት ተሸፍነው ስለሚታለፉ ኋላ ለወጣቶቹ ሕይወት እንቅፋት ይሆናሉ።እስከ ጋብቻቸው እለት ድረስ ራሳቸውን ጠብቀው ለመቆየት ፣ከጋብቻ በፊት በሚፈጸሙ ግንኝነቶች ላለመሰናከል ማወቅ የሚገቧቸውን ቁምነግሮች ባለመረዳታቸው ይጎዳሉ።አንዳንድ ጥናቶች እንደሚያመለክቱት ከሆነ ብዙ ወጣቶች ቅድመ ጋብቻ በሚፈጠሩ የግብረ ሥጋ ግንኝነቶች የሚመላለሱ ናቸው ።በዚህም ምክንያት የሚከሰቱ የተለያዩ እክሎች አሉ።በበሽታ መጠቃት፣የላጊዜና ያለ ዕድሜ ማርገዝ፣ያለጊዜ የተረገዘውን ጽንስ ማሰወረድ ፣ለማስወረድ በሚደረግ ሙከራም ሕይወትን ማጣት፣ከትምህርትና ከሥራ መስተጓጎል፤ከዚህ ሁሉ ነገር በኋላም በመነፈስ ጭንቀት መሰቃየት የጥፋተኝነት ስሜት መሰማት፣ወዘተ...  ሊጠቀሱ የሚችሉ ነገሮች ናቸው።


በዚህ አጭር ጽሑፍ እነዚህ ሁሉ ነገሮች ይቀረፉ ዘንድ ምን መደረግ አለበት የሚለውን ጥያቄ መመለስ በጣም አስቸጋሪ ነው።ይሁን እንጂ ትኩረት ከሚሹ ጉዳዮች መካከል አንዱን መዝዘን እናውጣ “ፍቅር”።የዚህ ጽሑፍ ዓላማ የተቃራኒ ጾታ ፍቅር በተለይም ከወጣትነትና ከመንፈሳዊነት አንጻር ያለውን  ገጽታና ሊኖረው የሚገባውን አካሄድ መመልከት ነው። “ፍቅር” የሚለው ቃል በብዙ ወጣቶች ዘንድ ተወዳጅ ቃል ነው።ከየንግግራቸው ውስጥ አይጠፋም።ቀልዳቸውና ጨዋታቸው ራሱ የሚሟሸው በርሱ ነው።አሁን አሁንማ በጣም የሚወደድ መብልና መጠጥ ላይ ሁሉ “በፍቅር የሚወደድ” የሚል ቅጥያ ይገባለት ይዟል።ይሁን እንጂ የቃሉ ትርጉም ትክክለኛውን ቦታ ባለማግኘቱ ወጣቶቹ ይጎዱበታል ።ወደ ቤተክርስቲያን የሚመላልሱት ወጣቶችም ምንም እንኳን ዘወትር ቃለ እግዚአብሔርን የሚሰሙ፣መዝሙር የሚያዳምጡ ቢሆኑም ወጣቶች ናቸውና ችግሩ እነርሱንም ይመለከታል።ጊዜ ሰጥቶ ለሚያዳምጣቸው፣የሚብሰለሰሉበትን ነገር ሊካፈላቸው ፈቃደኛ ለሆነ ሰው የሚያካፍሉት ቁምነገር ነው።በዚህም ምክንያት መንፈሳዊ ሕይወታቸው የሚበላሽባቸው ወንድሞችና እህቶች ጥቂቶች አይደሉም።ስለዚህ ችግሩ እነርሱንም የሚመለከት መሆኑን መገንዘቡ አስፈላጊ ይሆናል።

በወጣትነት ወቅት በተቀራኒ ጾታወች መካከል መሳሳብ ይኖራል።መሳሳብ ሁሉ ግን ለትዳር የሚያበቃ መሰረት ያለው፤በምንም ዓይነት ችግር የማይነዋወጥ በዐለት ላይ የተመሰረተ አይደለም።አብዛኛወቹ በጊዚያዊ መቀራረቦች ፣መተያየቶች “እኔስ ይህንን ለማድረግ ምን ይጎድለኛል?” ከሚሉ የወጣትነት ስሜቶች የሚፈጠሩ ናቸው ።በትምህርት ቤት የሚገናኙ፣በሰፈር የሚተያዩ፣በመነገድ የሚገናኙ ወዘተ ወጣቶች የሚፈጥሩት መቀራረብና “ወደድኩህ ወደድኩሽ” መባባል ሁሉ የሚዘልቅ ላይሆን ይችላል።ስለዚህ የወጣቶቹ መቀራረብ መፈቃቀር መሰረቱ ምን መሆኑን መረዳት ይሻል።ከዚህ በመነሳት በፍቅር ስም የሚጀመሩ አንዳንድ ግንኙነቶችን ከሚከተሉት ነጥቦች አንጻር ለመመዘን እንሞክራለን።

፩ የግብረ ሥጋ ግንኝነትን መሠረት ያደረገ ፍቅር
የአንዳንድ ወጣቶች ፍቅር መታወቂያው ያፈቀሩትን ሰው በሥጋ ለማወቅ የሚደረግ ችኩልነት ነው።ይወቁትም አይወቁትም ያለፈ ታሪኩ ምንም ይሁን ምን፣ግንኙነታቸው ነገ ችግር ይዞ ይምጣም አይምጣ የሚያስደስታቸው ካፈቀሩት ሰው ጋር በዝሙት መውደቅ ብቻ ነው ።በመጽሐፍ ቅዱሳችን የምናገኘው የአምኖንና የትዕማር ታሪክ ለዚህ አብነት መሆን ይችላል።አምኖን ከትዕማር ጋር በፍቅር በመጠመዱ ለመታመም ደርሶ ነበር።ነገር ግን ያለፈቃዷ ከክብር ካሳነሳት በኋላ ፍቅር ድራሹ ጠፋ ፤ይልቁንም የቀደመ ፍቅሩ በጥላቻ ተተካ በእውነት የአምኖን ፍቅር እውነተኛ ፍቅር ነበርን? እውነተኛ ፍቅርስ ከሆነ በቶሎ ወደ ጥላቻ ለመድረስ ያበቃው ምን ነገር ተፈጠረ? የአምኖን ፍቅር እውነተኛ አልነበረም። የዝሙት ፍላጎት እንጂ ። ዛሬም አንዳንድ ወጣቶች በዚህ አይነቱ አምኖናዊ ጾር በመነደፋቸው የሌላውን ሕይወት ለማበላሸት ላይ ታች ይላሉ።መነፈሳዊያን ወጣቶች ይህንን ልናስተውል ይገባል።ስለዚህ የምንወዳቸው ሰዎች ጠባይ በጊዚያዊ የሥጋ ፍላጎት ላይ የተመረኮዘ ከሆነ ፍቅራቸው ዘላቂ አለመሆኑን እንገነዘባለን።አበባውን ከቀጠፉ፣የፈለጉትን ካገኙ በኋላ አምኖናዊ ጠብያቸው ያገረሽባቸዋልና።

፪ በጊዚያዊ ጓደኝነት ላይ የተመሰረተ ፍቅር
በተለያዩ አጋጣሚዎች ከሰዎች ጋር መተዋወቅ መግባባት ሃሳብ ለሃሳብ ፣ንግግር ለንግግር መጣጣም ይኖራል።መግባባቶች ሁሉ ግን ወደ ትዳር ለመሄድ የሚያበቁ መሆን የለባቸውም። መጠናናት መለማመድ ፣ፈቃደ እግዚአብሔርን መጠየቅ ይገባል።አንዳንድ ወጣቶች ከመቀራረባቸው ብዛት የሚፈጠርን ጓደኝነት ለፍቅር በመስጠት ይሳሳታሉ። ለሳምንታትና ለወራት መለያየት እስከነመፈጠራቸው ሊያረሳሳቸው እንደሚችል ይዘነጋሉ።በጊዚያዊ መቀራረብ ላይ የሚፈጠር ፍቅርን መሠረት ያለው አድርጎ በማየት ነገን አርቆ ከመመልከት መከልከል አይገባም። በዚህ መልኩ ተጀምረው ለሠመረ ትዳር የበቁ ግንኙነቶች የሉም ለማለት ባይቻልም በአብዛኛው ሲታዩ ግን መጨረሻቸው ስለማያማር መንፈሳውያን ወጣቶች መጠንቀቅ ይገባቸዋል።

፫በኢኮኖሚና በስሜታዊ መረጋጋት ላይ የተመሠረተ ፍቅር
እንዲህ ዓይነቱ ፍቅር የያዛቸው ሰዎች ዓላማቸው ትዳር ላይ ያዘነበለ ነው።ከወጣትነት የዕድሜ ጣራ ያለፉ የትዳር መያዣ እድሚያቸው እያለፈ መምጣቱ የተሰማቸው ፣ቤትና ንብረት መያዝ ልጅ መውለድ እንዳለባቸው የሚሰማቸውና ብዙውንም ጊዜ “ምነው አግባ/ቢ እንጂ?” የሚሉ ጉትጎታዎች የበዙባቸው  ሰዎች ናቸው ።ጥሩ ገንዘብ ሥራ የእውቀት ደረጃ አላቸው።የሚፈልጉት ነገር ሁሉ ቢሟላላቸውም የጎደለ ነገር መኖሩ ስለሚሰማቸው ዕረፍት አይኖራቸውም።ያም የትዳር ጓደኛ ነው።ስለዚህ ያንን የጎደለ ነገር ለመሙላት ስለሚሹ ያገባሉ።የሚያገቡት ግን በምድራዊ ጥሪቱ የሚመስላቸውን ነው።የዚህ ዓይነት ሰዎች ፍቅር መለኪያው ያላቸው ምድራዊ ሃብትና የእውቀት ደረጃ በመሆኑ ፍቅሩ መሰረት ያለው ራስን ለሌላው አሳልፎ እስከ መስጠት ሊያደርስ የሚችል አይደለም።አንዳንዶቹም በገንዘብ ምክንያት በሚፈጠሩ አለመግባባቶች የሚበጣበጡ ፣ከትዳር ጓደኛ ውጪ በሚፈጸሙ ውስልትናዎች የተበላሹ ይሆናሉ።ስለዚህ ያፈቀርንበት ወይም የተፈቀርንበት ምክንያት ከምድራዊ ሃብትና እውቀት ውጪ መሆን አለመሆኑን ማረጋገጥ ይኖርብናል።

፬ ራስን ለሌላው አሳልፎ በመስጠት ላይ የተመሰረተ ፍቅር
ፍቅር ማለት ለራስ ምንም ሳይሳሱ ራስን ለተወዳጁ አሳልፎ መስጠት ነው፤ከእኔ ይልቅ የምወደው ሰው ይቅደም ማለት፤እኔ ቢደረግልኝ የምወደው ነገር ለምወደው ሰው ይደረግለት ማለት ነው።የተቃና መንፈሳዊ ትዳር መሠረት የሚሆነው ፍቅር ይህንን ያዘለ ነው።ነገር ግን ለምንወደው ሰው ራሳችንን አሳልፈን የምንሰጠው ምን ድረስ ነው? የሚለው ጥያቄ መመለስ አለበት።አንዳንድ ሰዎች መፈቀር አለመፈቀራቸውን ለማወቅ ራሳቸው ያማያደርጉትን ሊያደርጉትም የማይፈልጉትን ጥያቄ ይጠይቃሉ።የምትወደኝ/ጅኝ ከሆነ አድርግልኝ/ጊልኝ ይላሉ።ይህ ካልተደረገላቸው ያልተፈቀሩ ፤ከተደረገላቸው ደግሞ የተፈቀሩ ይመስላቸዋል። ይህ ግን የተሳሳተ የፍቅር መነገድ ነው። እውነተኛ ፍቅር በዚህ አይገለጽም።የዚህ ፍቅር ተጠቂ የሆኑ ወጣቶች ከአፍቃሪዎቻቸው በሚቀርቡላቸው የተሳሳቱ የመስዋዕትነት ጥያቄዎች ሕይወታቸው ይበላሻል።ማፍቀራቸውን በግልፅ ለማሳየት ክብረ ንጽሕናቸውን ቅድመ ጋብቻ የሚያቀርቡ ወጣቶች አያሌ ናቸው።ይሁን እንጂ ያሰቡት ቀርቶ ያላሰቡት ይተካና የፈለጉት ፍቅር በንቀት፣በጥላቻ፣ በኩራት ይተካል።ይህ በወደፊቱ ሕይወታቸው ላይ የሚያሳድረው ተጽዕኖ ቀላል አይሆንም።ስለዚህ መነፍሳውያን ወጣቶች ይህንን በመረዳት ቅድመ ጋብቻ የሚቀርቡ አላስፈላጊ መስዋዕትነቶችን መቃወም ይኖርብናል።በምድር በሥጋችን ፣በሰማይ በነፍሳችን ከሚጎዳ ነገር ራሳችንን እንጠብቅ።

፭በቅናት የታጠረ ፍቅር
የአንዳድን ወጣቶች ፍቅር ደግሞ መገለጫው ቅናት ነው ።ይህ ዓይነቱ በቅናት የታጠረ ፍቅር እውነተኛ ባለመሆኑ ለተፈቃሪዎች ሰላም የማይሰጥ ምድራዊ ገሃነም ነው።ሰዎች ያፈቀሩት ሰው ጥሩ ሲለብስ ሲያምርበት ከሰው ሁሉ ጋር ሲግባባ ፣በሰዎች ሲወደድ በስራው ከፍ ያለ ደረጃ ሲደርስ አይደሰቱም።የሚያመልጣቸው ይመስላቸዋል።ይጨነቃሉ።ስለዚህም ይቀናሉ።ቅናታቸው ከፍቅር የመነጨ መሆኑ እንዲታወቅላቸውም ይፈልጋሉ።የዚህ ዓይነቱ ፍቅር መሠረቱ በአብዛኛው ውጫዊ ተክለ ቁመና ነው ።ውስጣዊ ውበት ቦታ የለውም።ታይቶ የሚጠፋ አፍአዊ ነው።ያ አፍአዊ ውበት ሲደበዝዝ ወይም ከዚያ የበለጠ ሲገኝ ይቀራል ይሻራል።

ወጣትነት የነገው ማንነት የሚጣልበት መሠረት ነው።በወጣትነት የተበላሸን ሕይዎት ለማረቅ በጣም አስቸጋሪ ነው ።ከነዚህ የወትሃቶች ሕይወት ከሚበላሹባቸው ነገሮች መካከል ደግሞ ከተቃራኒ ጾታ ጋር የሚኖረን ፍቅር አንዱ መሆኑን ከላይ ተመልክተናል።ስለዚህም ከፍተኛ ጥንቃቄ ማድረግ ይኖርብናል።በወትሃትነት የሚመጡ ፍላጎቶችን ሁሉ ማስተናገድ አይገባም።ያለጊዚያቸው ከመጡ ፈተናዎች ናቸውና ልንቃወማቸው ይገባል።ከሁሉ አቀድሞ ራሳችንን ለመቻል መጣር ሕይወታችንን በመንፈሳዊ ሕይወት ማጎልመስ ይገባናል።በዚህም ምክን ያት ከሚመጡ የጎልማሳነት ምኞቶች መራቅ የምንችለው  ይህንን ስንረዳ ብቻ ነው ።፪ጢሞ፪፥፳፪ በአጠቃላይ በፍቅር ሰበብ የሚመጡብንን ፈተናዎች ለመቋቋም እውነተኛውን ከሐሰቱ ለመለዬት እንጣር ፈቅደ እግዚአብሔርንም እንጠይቅ።የቅዱሳን አምላክ እግዚአብሔር ይርዳን።አሜን።

ምንጭ፦ፈሬ ሊቃውንት
           

No comments:

Post a Comment