Wednesday, July 19, 2017

እርሳኝ አትበይኝ

በድል ያሳለፍሽኝ የሞትን አደጋ፣
እንዳይ የረዳሽኝ የህይወትን ዋጋ፣
የልፋት ደሞዜን የተጋድሎን ፀጋ፤
በውለታሽ ብዛት ያረግሽኝ ባለዳ፣
የመስከረም አደይ ውቧ ጽጌረዳ ፣
ልቤን ያሸፈትሽው ገና በማለዳ፤
ፍቅርን የሰጠሽኝ ጠቅልለሽ በሸማ፣
ስምሽ በአንደበቴ ከፍ የሚል ከማማ፤
ከእንቅልፍ የሚያነቃኝ የጉርሻሽ ትዝታ፣
ድምጽሽ ሚያባንነኝ ሁሌም ጥዋት ማታ፤
ከብርንዶ ይልቅ ሽሮሽ ሚናፍቀኝ፣
አንች በሌለሽበት ወለላ የሚያንቀኝ፤
ተዳፍነሽ የቀረረሽ የልቤን ውስጥ እሳት ፣
እንዴት ይቻለኛል እኔ አንቺን ለመርሳት?
አበባ ጥርሶችሽ ከኔ ይሰንብቱ፣
ሳቅና ጨዋታ ዝና የሚያውቁቱ፤
ብዬ ያዜምሁልሽ የሀሴት ዝማሬ፣
በናፍቆትሽ ብርታት ስባዝን አድሬ፤
አምባገነን ሥልጣን ከላይ የተቸረው ፣
መተተኛ ዲያቆን አንደበቴን  ቢያስረው፤
ማሰንበት ቢቻለው ጭድን ከእሳት ጋራ፣
ማስታረቅ ቢያውቅበት ሸማን ከገሞራ፣
በአንቺ እና እኔ መሀል ቢያፈልስ ተራራ፣
መውደዴን ባልነግርሽ ቢያዝ አንደበቴ፣
እርሳኝ አትበይኝ አይችልም አንጀቴ።
ፍቅሬን ባልገልጽልሽ ቢዘጋ ልሳኔ፣
እርሳኝ አትበይኝ ችሎ አይችልም ጎኔ።

©ጌች ቀጭኑ ለY.F ሐምሌ 12/2009 .

No comments:

Post a Comment