Friday, October 30, 2015

መለየት

የለም! የለም!
መለየት መሞት አይደለም፣
ሞትም መለየትን አያክለው ፣
መለየትም ሞትን አይመስለው፣
ትርጓሜአያቸው ለየቅል ነው፣
አንቺም እኔም ጅረት ሆነን፣
ከራሳችን ምንጭ ፈልቀን፣
በራሳችን ፈለግ ፈሰን፣
ህይወት በሚሉት መቅበዝበዝ
አገር ምድሩን አዳርሰን፣
ሄደን!ሄደን! ሄደን! ሄደን!
ወርደን!ወርደን!ወርደን!ወርደን!
ሞት በሚሉት ውቅያኖስ
አንድ ስንሆን ተዋህደን
ተገናኘን እንበል እንጅ
መች ጨርሰን ተለያየን
      የለም!የለም!
መራቅ መለየት አይደለም፣
ሰው በሰወች ግዞት፣
ችግር ይዞት፣
አገር ቀየውን ጥሎ፣
ስልቻውን በጫንቃው አዝሎ፣
ቅሉን ጨርቁን አንጠልጥሎ፣
ብቻውን ሄደ ቢለው ሰፈርተኛው ተጃጅሎ፣
እርሱ በልቡ ህንጻ በማይዘመው በማይፈርሰው፣
 ከተጓዘ አኑሮ ሰው፣
እውን ይሄ መለየት ነው
የለም! የለም!
መለየት ይህ አይደለም
ትርሚያቸውን እንቀይረው፣
ላንቺ እና ለኔ ሌላ ነው፣
ከፊቴ ቁጭ ብለሽ
ከፊትሽ ቁጭ ብየ፣
ክንድሽን ካንገቴ ጥለሽ
ክንዴን ካንገትሽ ጥየ፣
የምታወሪው ሳይገባኝ
ራሴን ስነቀንቅ፣
የማወራሽ ሳይገባሽ
ለይስሙላ ጥርስሽ ሲስቅ፣
ቻው ቻው ሲለኝ ቀልብሽ፣
ደህና ሁኚ ሲልሽ አይኔ፣
መለየት ይህ ነው ለኔ።

No comments:

Post a Comment